ሳሞጤስ ዲስ1490 ዓ.ም. አኒዩስ ዴ ቪቴርቦ የተባለው ጣልያናዊ መነኮሴ ባሳተመው ዜና ማዋዕል ዘንድ የኬልቶች (በጋሊያ፣ አሁንም ፈረንሳይ አገር) መጀመርያ ንጉሥና አባት ነበረ። የያፌት ልጅ ሲሆን ለ157 ዓመት (2420-2263 ዓክልበ. ግድም) እንደ ነገሠ ተብሏል።

አኒዩስ እንዳለው፣ የባቢሎን ታሪክ ጸሓፊ ቤሮሶስ (290 ዓክልበ.) ስለ ኖኅ ልጆች ብዙ ጥንታዊ መዝገቦች አቅርቦ ነበር። በዚህ በኩል፣ በናምሩድ 13ኛው ዓመት ሳሞጤስ ኬልታ ወይም ጋሊያ በተባለው ክፍል ሠፈረ። ይህም ከራይን ወንዝና ከፒረኔስ ተራሮች መካከል ያለው ሁሉ ከነብሪታንያ ደሴቶች ጠቀለለ። አገሩም መጀመርያ ከርሱ ስም «ሳሞጤያ» ይባል ነበር። በዚህ ዘመን ከሳሞጤስ ይልቅ ጥበበኛ ሰው አልነበረም ብሎ ይጨምራል። ለ112 አመት ከነገሠ በኋላ ደግሞ ሕግጋት ለአገሩ አወጣ። ከረጅም ዘመኑ በኋላ ልጁ ማጉስ እንደ ተከተለው ይላል።

በ1520 ዓ.ም. ግድም የጻፈው ጀርመናዊ መምህር ዮሐንስ አቨንቲኑስ እንዳለው የባቢሎን ግንብ በተሠራ ጊዜ ናምሩድ የካም ልጆች መሪ ሲሆን፣ ዲስ ሳሞጤስ ለያፌት ልጆችና ኢስተር (ዮቅጣን) ለሴም ልጆች 3 መሪዎች ነበሩ። በፕሲውዶ-ፊሎ (100 ዓ.ም. ግድም) ሦስቱ መሪዎች ናምሩድ፣ ዮቅጣንና ለያፌት ወገን የሮድኢ ልጅ «ፌኔቅ» ይባላሉ፤ በፔትሩስ ኮመስቶር (1165 ዓ.ም.) ሦስቱ መሪዎች ናምሩድ፣ ዮቅጣንና ለያፌት ወገን «ሱፌኔ» ወይም «ሱስቴኔ» ይባላሉ።

ራፋኤል ሆሊንስሄድ (1569 ዓ.ም.) ይህ የያፌት ልጅ ሳሞጤስ መታወቂያና የሞሳሕ ማንነት (ከኦሪት ዘፍጥረት 10 ታውቆ) አንድላይ እንደ ነበር የሚል ሃልዮ አቀረበ። ዘሬ ግን አብዛኛው መምህሮች የአኒዩስ ጽሑፍ በሙሉ እንደ ሐሣዊ መረጃ ይቆጥሩታል።

ከአኒዩስ በፊት ስለ ሳሞጤስ አንዳንዴ የሚጠቀስ ማስረጃ ጥቂት ብቻ ነው። በ3ኛው ክፍለ ዘመን ዓ.ም. የጻፈው ግሪክ ጸሐፊ ዲዮገኔስ ላኤርቲዮስ ስለ ድሩዊዶች (የጥንታዊ ኬልቶች አረመኔ ቄሳውንት) ሲተርክ፣ ከክፍሎቻቸው አንዱ «ሰምኖጤስ» እንደተባለ ጽፏል። በ1ኛው ክፍለ ዘመን ዓክልበ. ደግሞ የሮሜ ንጉሥ ዩሊዩስ ቄሣር በመጽሐፉ እንደ ገለጸው፣ ኬልቶቹ (ጋሎቹ) ወላጃቸው አምላኩ «ዲስ ፓተር» (ዲስ አባት) እንደ ነበር ያምኑ ነበር።

ቀዳሚው
የለም
የሳሞጤያ (ጋሊያ) ንጉሥ
2420-2263 ዓክልበ. ግድም (አፈታሪክ)
ተከታይ
ማጉስ