ጌሤም (ዕብራይስጥ፦ גֹּשֶׁן /ጎሼን/፤ ግሪክኛ፦ ጌሤም) በብሉይ ኪዳን መሠረት በታችኛ (ስሜናዊ) ግብፅአባይ ወንዝ አፍ ሠፈር በዮሴፍ ዘመን የዕብራውያን (እስራኤላውያን) መኖርያ ክፍላገር ሆነ።

ዮሴፍ በኦሪት ዘፍጥረት ፵፭፡፲ የጌሤም ሠፈር ለአባቱ ያዕቆብ ቤተሠብ ሠጠው። ዕብራውያን በዚህ ዘመን በከነዓን ያደሩ ዕረኞች ነበሩ። ታላቁ የ፯ ዓመት ረሃብ በከነዓን በደረሰበት ዘመን የያዕቆብ ልጅ ዮሴፍ በግብጽ የፈርዖን ጥበበኛ ጠቅላይ ሚኒስትር ስለ ሆነ ወደዚያ አገር ፈለሱ።

በ፵፯፡፮ «ፈርዖን» ለዮሴፍ እንዲህ ይላል፦ «የግብፅ ምድር በፊትህ ናት፤ በመልካሙ ምድር አባትህንና ወንድሞችህን አኑራቸው፤ በጌሤም ምድር ይኑሩ፤ ከእነርሱም ውስጥ እውቀት ያላቸውን ሰዎች ታውቅ እንደ ሆነ በእንስሶቼ ላይ አለቆች አድርጋችው።» ከዚህ በኋላ የእስራኤል ነገዶች በጌሤም ዕጅግ በለጠጉ፣ በምድሩም በዙ።

የ14ኛው ሥርወ መንግሥት ግዛት

ዮሴፍ ከዓረፈ በኋላ እስራኤላውያን በአገራቸው ዕጅግ ኃይለኛና ሀብታም ባለሥልጣኖች ሆኑ። ዳሩ ግን መጽሐፈ ኩፋሌ እንደሚገልጸው የዛኔው የግብጻውያን ፈርዖን ከከነዓን ንጉሥ መምከሮን ጋር ጦርነት እየዋጀ ሲገደል፤ እነዚህ ከከነዓን የደረሱት እረኞች በግብጻውያን ዘንድ በጥርጣሬ ይታዩ ጀመር። ስለዚህ በኋላ በነገሠ ፈርዖን ትዕዛዝ ዕብራውያን የግብጻውያን ባርዮች (የሕንጻ ሠራተኞች) ተደረጉ። ሙሴ በተወለደበት ዘመን የነገሠው ፈርዖን በተለይ ጨካኝ እርምጃ በዕብራውያን ላይ ወሰደ፤ ይህም የዕብራውያን ወንድ ጨቅላ ሲወለድ ወደ አባይ እስከ መጣላቸው ድረስ ሆነ። ዳሩ ግን ኦሪት ዘጸዓት እንደሚተርክ ሙሴ በእናቱ እርዳታ ይህን አመለጠ፤ አድጎም ሕዝቡን ሁሉ ከግብጽ ባርነት ወደ ከነዓን (በ፵ ዓመት ላይ) መራቸው።

ሴማዊ ቤተሠቦች ከከነዓን ወደ ግብጽ ሲደርሱ በኻይከፐሬ 2 ሰኑስረት ዘመነ መንግሥት

በዕብራይስጡ መጽሐፍ ቅዱስ ዕብራውያን በጌሤም ለ፬ መቶ ዓመታት ቆዩ ሲለን በሌሎች ጥንታዊ ትርጉሞች ግን ፬ መቶ ዓመት በከነዓን (ከካራን ወጥተው) እና በግብጽ የዋሉበት ዘመን አንድላይ ነው። በመጽሐፈ ኩፋሌ ያለው ዜና መዋዕል ዘንድ ከግብጽ ታሪክ ጋር ሲነጻጽር ታላቁ ረሃብ በ2171 ዓመተ ዓለም (1900 ዓመታት ከክርስቶስ ልደት በፊት ዓ.ም.) የደረሰው ነው፤ በሚከተለውም ዓመት ነገዶቹ ወደ ጌሤም ወረዱ። በ2193 ዓ.ዓ. (1878 ዓክልበ.) ያዕቆብ በግብፅ ዓርፎ በከነዓን ተቀበረ። በ2244 ዓ.ዓ. (1827 ዓክልበ.) ዮሴፍ ዓረፈ። ከዚህ ትንሽ በኋላ በታችኛ ግብጽ 14ኛው ሥርወ መንግሥት በመጀመርያ ፈርዖናቸው በያክቢም ሰኻኤንሬ የተነሣበት ዘመን ልክ ይስማማል። እነርሱ በግብጻውያን ፈቃድ በጌሤም አካባቢ የነጋዴዎች ሠፈር እንዳስተዳደሩ ይመስላል። የግብጻውያን ጦርነት ከከነዓን ንጉሥ መምከሮን ጋር በ2263 ዓ.ዓ. (1808 ዓክልበ.)፤ የሙሴም ልደት በ2330 ዓ.ዓ. (1741 ዓክልበ.)፤ ዘጸአት በ2410 ዓ.ዓ. (1661 ዓክልበ.) ደረሰ።

በዘፍጥረት በአንዳንድ ሥፍራ ጌሤም «ራምሴ» ይባላል። ስለዚህ ብዙ ሊቃውንት ዘጸዓት በግብጽ ፈርዖን 2 ራምሴስ ዘመን (1287-1221 ዓክልበ.) እንደ ተከሠተ ይገምታሉ። ሆኖም ከዚህ ዘመን እስከ ዳዊትሰሎሞን መንግሥት ድረስ ያለው ጊዜ ለእብራውያን ዘመነ መሳፍንት አይበቃም።