ነጭ ሽንኩርት (Allium sativum) የሽንኩርት ዘመድ ሲሆን ለምግብም ሆነ ለመድኅኒት በሰፊ የሚጠቀም ዕፅ አይነት ነው። በጣም ጠንካራ ጣዕም አለው።

ነጭ ሽንኩርት

አስተዳደጉ በጣም ቀላል ነው፤ በእፃዊ ተዋልዶ ይበዛል። የሚተከለው የአኮራቹ ክፍሎች እራሳቸው እንጂ ዘር አያሰፈልግም። በብዙዎች አገራት፣ የአኮራቹ ክፍሎች በመፀው ወራት (ከበረድ ወቅት አስቀድሞ) በላይ አፈር ውስጥ ተቀብረው በሙቀት ጊዜ ይታረሳል። በውርጭ እንዳይበላሽ ቢያንስ በ፫ ኢንች ጥልቀት ይቀበራል። እንግዲህ ከተቀበረው በኋላ በስምንት ወር ያህል ይመረታል። እያንዳንዱ ክፍል በመሬት ውስጥ አዲስ አኮራች እንደ ፈጠረ ይሆናል።

ነጭ ሽንኩርት ለማሳደግና ለማብዛት ለሕፃን ቢሆንም እጅግ ቀላል በመሆኑ፣ ምናልባት የሰው ልጅ ከሁሉ በፊት ያስለመደው ተክል ዝርያ ሊሆን ይችላል፤ እንዲሁም የምጣኔ ሀብት መጀመርያ መሠረት ሊባል ይቻላል። በጥንታዊ ግብጽ ሠራተኞች ከፈርዖን መንግሥት የነጭ ሽንኩርት፣ ሌላ ሽንኩርት ወዘተ. መቁነን በየቀኑ ይቀበል ነበር። ይህም ለምግብ፣ እንዲሁም አንድላይ ለገንዘብና ለዘር (ለማትረፍ) ያገልግል ነበር። ለመንግሥት የተመለሰውም ግብር (በሽንኩርት ወዘተ. ተከፍሎ) ለደህንነት በፒራሚድ መዝገቦች ውስጥ ይከማች ነበር።

ከጥንት ጀምሮ ለጤንነት እጅግ መልካም መሆኑ ታውቋል። ለጉንፋንና ለብዙ ሌላ አይነት ሕመም በማከም ይስማማል። በተለይ የደም ጋንን ከዝቃጭ መጥራት ስለሚችል፣ ለልብ ጤናማ ሆኖ ይቆጠራል። በብዙ አገራት ለረጅም ዘመን በቆየ እምነት፣ ነጭ ሽንኩርት ክፉውን ያሳድዳል።

አኮራቹም ለወባ ወይም ለሆድ ቁርጠት መበላቱ በደብረ ሊባኖስ ዙሪያ ጥናት ተዘገበ። እንዲሁም ለሆድ ቁርጠት ከፌጦ ጋር ሊበላ ይችላል፣ ወይም ከጤና አዳም ፍሬና ቅጠል፣ ጠጅ ሳር ሥርና ኣጣጥ ቅጠል ጋር ሊበላ ይችላል።።[1]

ፍቼ ኦሮሚያ በተመሳሳይ ጥናት፣ ነጭ ሽንኩርት በማርና በበርበሬ ለወባ ወይም ለትል ይበላል።[2]

ዘጌ ጣና በተመሳሳይ ጥናት፣ ነጭ ሽንኩርት ለ«ዓይነ ማዝ» ይቀባል።[3]


  1. ^ በደብረ ሊባኖስ ዙሪያ ያለው ሕዝብ መድሃኒታዊ እጾች እውቀናና ጥቅም 1998 ዓም ከጥላሁን ተክለሃይማኖት፣ ሚሩጸ ጊዳይ፣ ግርማይ መድኅን፣ ያለም መኮነን፣ አዲስ አበባ ዩኒቬርሲቴ፣ አክሊሉ ለማ ተቋም
  2. ^ የፍቼ፣ ኦሮሚያ ባህላዊ መድሃኒት ጥናት 2006 ዓም ከዓቢዩ እኒየው እና ሌሎች፣ ጎንደርና አዲስ አበባ ኡኒቨርሲቲዎች ሥነ ፍጥረት ኮሌጆች
  3. ^ የዘጌ ልሳነ ምድር ባህላዊ መድሃኒት ጥናት 1999 ዓም ከጥላሁን ተክለሃይማኖት፣ ሚሩጸ ጊዳይ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ