ማጫ በጥንት በየትም አገር አሁንም በብዙ ኅብረተሠቦች የሚገኝ የጋብቻ ልማድ ወይም ሕግ ነው።

ታሪክ ለማስተካከል

መስጴጦምያ ለማስተካከል

የጥንቱ መስጴጦምያ ሕግጋት ማጫን ይቀምሩ ነበር። ማንም ወንድ ያልታጨችውን ሴት ማግባት ከወደደ፣ ማጫን ለሴቲቱ አባት ለመክፈል ነበረበት። በዚያ ወቅት መሐለቅ ገና ስላልተፈጠረ፣ መደበኛ የንግድ ገንዘቦች በተለይ ብርገብስ ወይም ከብት ነበሩ። ይህም ተዋውሎ ተከፍሎ አማቱ ግን በኋላ ስምምነቱን ከሰበረበት፣ ቁም ነገር ነበር፤ አማቱ ፪ እጥፍ ማጫ ለሰውዬው መመልስ ተገደደ (የኡር-ናሙ ሕግጋት §15፤ የሊፒት-እሽታር ሕግጋት §29፤ የኤሽኑና ሕግጋት §25፤ የሃሙራቢ ሕግጋት §160-161)። በሃሙራቢ ሕጎች ደግሞ፣ አማቹ ሀሣቡን ቀይሮ ልጂቱን እምቢ ቢላት፣ ማጫው አይመለስለትም በማለት ይወስናል (§159)።

ስምምነቱ ጸንቶ እጮኞቹ ከተዳሩ ወደ ቤቱ ስትገባ፣ አማት ለአዲሱ ቤተሠብ ጥሎሽን ይሰጥ ነበር። ጥሎሽ በዘልማድ ከማጫው መጠን ይበልጥ ነበር። ጥሎሽን መስጠት ግዴታ አልነበረም፤ ካልተሰጠ ግን በአማቱ ዕረፍት ልጂቱ ከወንድሞቿ ጋራ ሙሉ ድርሻ ርስት ትቀበል ነበር (ሃሙራቢ §180)። ምንም ወራሽ ልጅ ሳይወልዱ አንዱ ባለትዳር ያረፈ(ች) እንደ ሆነ፣ አማትዬው ጥሎሹ እንዲመለስለት ይግባኝ ማለት ቻለ (ኤሽኑና §17-18፤ ሃሙራቢ §163)።

እስራኤል ለማስተካከል

ሕገ ሙሴ ያህዌ ተመሳሳይ የማጫ ሥርዓት ለእስራኤል መሠርቷል። ወንዱ ካልታጨችው ሴት ጋር በወሲብ የተኛ እንደ ሆነ ደግሞ፣ የ50 ሰቀል ብር (500 ግራም ያህል) ማጫ ለአባትዋ ይክፈልና ዕድሜ ልክ ሚስቱ ትሁን በኦሪት ዘዳግም 22:28 ይገለጻል። አባትዋም ሴት ልጁን ለዚህ ሰው መስጠት እምቢ ቢልም፣ ሰውዬው ግን ብሩን መክፈል አለበት (ኦሪት ዘጸአት 22:17)።

እስልምና ለማስተካከል

እስልምናቁራን መሠረት ባል ሚስትን ሲያግባት ማጫን ወይም መኅርን እንዲሰጣት ግዴታ ነው። በአብዛኛው ትምህርቶች ዘንድ የዚህ ስጦታ ዋጋ ማንኛውም ዋጋ ሊሆን ይችላል፤ በሌሎች አስተሳሰቦች ግን ቢያንስ ፲ ወይም ፫ ድርሃም መሆን አለበት። ይህ ማጫ ከባል በቀጥታ ወደ ሚስት የሚከፈል ነው እንጂ ዐማቶች በነገሩ አይገቡም። በሁለት ድርሻዎች አንዱም በሠርግ ጊዜ የተረፈውንም ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ሊከፈል ይችላል።

ማሊ መንግሥት ኩሩካን ፉጋ መሠረት፣ አንድ ላም ለሴቲቱ፣ አንድም ለአባቷ፣ አንድም ለእናቷ እንደ ማጫ ያስፈልጋል።

ፍትሐ ነገሥት ለማስተካከል

ተመሳሳይ የማጫ መርኅ በፍትሐ ነገሥት ምዕራፍ 24 ክፍል ፫ ይታያል። ማጫው የሚከፈለው ወደ እጮኛይቱ ቤተሠብ እንደ ሆነ፣ በኋላም አድጋ ለጋብቻው እምቢ ካለች፣ ፪ እጥፍ ማጫ መመልስ ሊገደዱ ይቻላል። በቀጥታ ወደ ሴቲቱ የሚሰጠው ማጫ ግን ለባልዋም ደህንነት መሆኑ ይወሰናል።