1 ላባርና እንደሚታሠብ ምናልባት 1582-1559 ዓክልበ. አካባቢ ከሕሽሚ-ሻሩማ በኋላ በኩሻራ (በሐቲ) አገር) የገዛ ንጉሥ ነበር።

ላባርና የወረሱት (ቀይ) እና የያዙት (አረንጓዴ) አንዳንድ ከተሞች

1 ሐቱሺሊ አዋጅ ውስጥ (1559 ዓክልበ.) የላባርና ተከታይ ሐቱሺሊ እንዲህ ይላል፦

.«...የንጉሥ ቃል የሚሰብር ፈጽሞ ይሙት።... ያውም ከአያቴ ሕሽሚ-ሻሩማ ቃል ነው። ልጆቹ ወደ ሌላው ወገን አልዞሩም? አያቴ በሻናኊታ ከተማ ላባርናን እንደ ልጁ ሰየመው። በኋላ ግን አገልጋዮቹም አለቆቹም ትዕዛዙን ተሰናከሉ፣ ፓፓሕዲልማሕንም ዘውድ ጫኑ። ግን ስንት ዓመት አለፉ? ስንት አመለጡ? የአለቆቹ ቤቶች የት አሉ? አልሞቱም?»

ከዚህ የተነሣ፣ ንጉሥ ሕሽሚ-ሻሩማ ላባርናን በጉዲፈቻ እንደ አልጋ ወራሽ እንደ ሾመው ይታስባል። የሕሽሚ-ሻሩማ ልጆች እንዳመጹበትና ከነሱ መሃል ፓፓሕዲልማሕ የተባለው ለአጭር ጊዜ (1582 ዓክልበ. ግ.) ዙፋኑን እንደ ቃመው ይመስላል። ሆኖም የላባርና ወገን ፓፓሕዲልማሕን ድል አድርጎ እንደ ሕሽሚ-ሻሩማ ፈቃድ ላባርና መንግሥቱን ወረሰ።

ኬጥያውያን መስዋዕት ዝርዝር ላይ፣ ሕሽሚ-ሻሩማ የላባርና አባት ይባላል። ከፊተኛው ሰነድ እንዳየነው ግን ላባርና ልጁ የሆነው በጉዲፈቻ እንደ ነበር ይመስላል።

የተለፒኑ አዋጅ (1483 ዓክልበ. ግ.) ደግሞ ስለ ላባርና ይተርካል፦

«...ቀድሞ ላባርና ታላቅ ንጉሥ ነበር። ልጆቹ፣ ወንድሞቹ፣ ዘመዶቹ፣ ጭፍሮቹ አንድ ላይ ነበሩ። ሀገሩ ትንሽ ነበረች፣ ሆኖም በማናቸውም ዘመቻ ቢሄድ፣ የጠላቱን ምድር በኃይሉ ተገዥ አደረገ። ምድሮቹን አንድ በአንድ አጠፋቸው። ምድሮቹን አደከመ፣ የባሕር ጠረፎች አደረጋቸው። ከዘመቻ ሲመልስ፣ ከልጆቹ እያንዳንዱ ወደ ገዛው ምድር ሄደ። ሑፒሽና (ኩቢስትራ) ከተማ፣ ቱዋኑዋ (ቱዋና) ከተማ፣ ነናሻ ከተማ፣ ላንዳ (ላራንዳ) ከተማ፣ ዛላራ ከተማ፣ ፓርሹሐንታ (ቡሩሻንዳ) ከተማ፣ ሉሽና (ሉስትራ) ከተማ፤ እያንዳንዱ ምድር እየገዙ ታላላቆቹ ከተሞች ይበልጸጉ ነበር።...»
የላባርና (1፣ ብጫ)፣ የ1ሐቱሺሊ (2)ና የተለፒኑ (3) ግዛቶች ስፋት ያህል

የላባርና ልጆች የገዙት ከተሞች ሁሉ በማዕከለኛ አናቶሊያ ይገኛሉ። በሌላ ምንጭ ዘንድ ወደ ምዕራብ ከአርዛዋ (ሉዊያ) አገር አንዳንድ ቦታ እንደ ያዘ ይታወቃል። ወደ ደቡብም በመድቴራኔአን ላይ ያለው አገር አዳኒያ (በኋላ ኪዙዋትና እና ኪልቅያ የተባለው) ከሐቱሺሊ ዘመን በፊት ለሐቲ እንደ ተገዛ ይመስላል።

የላባርና ንግሥት ታዋናና ተባለች። በኋላ «ላባርና / ታባርና» እና «ታዋናና» የሚሉ ስያሜዎች እንደ ነገሥታት ማዕረጎች (እንደ ሮማይስጥ) ቄሣር) ይቆጠሩ ነበር። እንዲሁም ተከታዩ ንጉሥ 1 ሐቱሺሊ ደግሞ «2 ላባርና» በመባል ታውቀዋል፤ ስለዚህ ይህ ላባርና በዘልማድ «1 ላባርና» ይባላል።

ተከታዩም ሐቱሺሊ በአንዱ ሰነድ እራሱን «የንግሥት ታዋናና ወንድም ልጅ» ይላል። ሕሽሚ-ሻሩማን አያቱን ስላለው፣ ታዋናና እራሷ የሕሽሚ-ሻሩማ ልጅ ስትሆን ባልዋ ላባርና በዚያ አልጋ የሕሽሚ-ሻሩማ ወራሽ እንደ ሆነ ይታስባል።

በድሮ ታሪክ ጸሐፊዎች እንደ ሂውጊኑስ (1 ዓም አካባቢ)፣ ቅዱስ ጄሮምቅዱስ አውግስጢኖስኦሮሲዮስ (400 ዓም. አካባቢ) ወዘተ.፣ በዚያው ዘመን ያሕል «ሊበር ፓተር» (ሊበር አባት) የተባለ ንጉሥ «ሕንድ»ን ሁሉ በጨካኝ ጦርነት አሸነፈ፤ «ኒሳ» የተባለ ከተማ መሠረተ። በጣልያን በ194 ዓክልበ. የተገነነው አረመኔ ሥነ ስርዓት በዚህ «ሊበር ፓተር» ትውስታ ይካሄድ ነበር፤ ከዚያም በሮማይስጥ ቃላት እንደ «ሊበርታስ» (አርነት) ወደ ሌሎች ቋንቋዎች ገብቷል። በዘመናት ላይ በምሥራቅ ወይም በእሥያ ያሉት አገራት ሁሉ በመሳሳት «ህንድ» ሊባሉ ቻለ። «ኒሳ» ግን ካነሽ ሊሆን ስለሚችል ምናልባት የ«ሊበር» መታወቂያ ከዚሁ ንጉሥ ላባርና ትዝታ እንደ ደረሰ ይቻላል።

ቀዳሚው
ሕሽሚ-ሻሩማ
ሐቲ ንጉሥ
1582-1559 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
1 ሐቱሺሊ