፩ ሑዚያ በ1488 ዓክልበ. አካባቢ ከአባቱ ከአሙና በኋላ በሐቱሳሽ (በሐቲ አገር ወይም የኬጥያውያን መንግሥት) የገዛ ንጉሥ ነበር።

የቀዳሚው አሙና ፫ኛ ልጅ ሲሆን ሁለቱ ትልልቅ ወንድሞቹ ተገድለው እሱ ለአጭር ጊዜ ንጉሥ ሆነ። ይህን የምናውቀው ተከታዩ ተለፒኑ በጻፈው የቴሌፒኑ ዐዋጅ በተባለው ሰነድ ይተረካል።

«[...] አሙናም ደግሞ አምላክ ሊሆን ሲል፣ የንጉሣዊ ዘበኞች አለቃ ዙሩ በምስጢር ከገዛ ቤተሠቡ ልጁን ታሑርዋይሊን፣ «የወርቃማው ጦር ሰውዬ» የተባለውን፣ ልኮ እርሱ የቲቲያን (የአሙና በኲር) ቤተሠብ ከነልጆቹ ገደላቸው።
መልእክተኛውንም ታሩሕሹን ልኮ እርሱ ሐንቲሊን (የአሙና ፪ኛ ልጅ) ከነልጆቹ ገደላቸው። ሑዚያም ንጉሥ ሆነ፣ ተለፒኑም ዋና ኢኅቱን ኢሽታፓሪያን አገባ። ሑዚያ እነሱንም ሊገድላቸው ይፈልግ ነበር፣ ሆኖም ጉዳዩ ስለ ተገለጸ ተለፒኑ አባረራቸው።
ወድሞቹ አምስት ነበሩ፣ ቤቶችንም ሠራላቸው፤ ይኑሩ፣ ይብሉ፣ ይጠጡ አለላቸው፤ ማንም አይበድላቸው! ተደጋግሜ እናገራለሁ፣ እነሱ በደሉኝ፣ እኔስ አልበድላቸውም።»
[...]
«እኔ ንጉሡ (ተለፒኑ) ሳላውቀው፣ የምርኳዝ ተሸካሚ ታኑዋ ሑዚያንና ወንድሞቹን ገደላቸው። እኔ ንጉሡ ስሰማው፣ ታኑዋን፣ ታሑርዋይሊንም፣ ታሩሕሹን አምጥተው ጉባኤው መሞት ፈረደባቸው። እኔ ንጉሡ ግን ለምን ይሙቱ? ዓይናቸው ይሠውሩ! ብዬ፣ እኔ ንጉሡ በውነት ገበሬዎች አደረግኋቸው። የጦርነት መሣርያ ከጫንቃቸው ወስጄ ቀንበር ሰጠኋቸው!»

በዚሁ ታሪክ፣ ዙሩ «የንጉሥ ዘበኞች አለቃ» ሲባል ይህ ማዕረግ ለንጉሥ ወንድም እንደ ተሰጠና ዙሩ ታዲያ የአሙና ወንድምና የ1 ዚዳንታ ልጅ እንደ ነበር ይታመናል። ልጁም ታርሑዋይሊ «የወርቃማው ጦር ሰውዬ» ደግሞ ወደፊት ንጉሥ ሆነ። ዙሩ ቀዳሚ ወራሾቹን ቲቲያንና ሐንቲሊን ያስገደላቸው ለአሙና ሦስተኛው ልጅ ሑዚያ ወራሽነት እንዲያገኝ እንደ ነበር ይታስባል።

በሑዚያ ዘመን ግን በቅርቡ ሑዚያ ደግሞ እኅቱን ልዕልት እሽታፓሪያንና ባለቤቷን ተለፒኑን ለመግደል አሰበ፣ ይህም ስኬታም አልሆነምና በተቃራኒ ተለፒኑ ሑዚያን ከግቢው አባረረው። ተለፒኑ ከቀዳሚዎቹ ይልቅ ሩኅሩኅ ይመስላል፤ ለሑዚያ ይቅርታ ሰጠ፣ በኋላም ሑዚያ ሲገደል ለሑዚያ፣ ቲቲያና ሐንቲሊ ገዳዮች ይቅርታ ሰጥቶ የእርሻ ሥራ አስገደዳቸው ይላል።

ቀዳሚው
አሙና
ሐቲ ንጉሥ
1488 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
ተለፒኑ