ካልቡምሱመራዊ ነገሥታት ዝርዝር ላይ የኪሽ 2ኛው ሥርወ መንግሥት ንጉሥ ነበረ። የማማጋል (መርከበኛው) ልጅ ሆኖ ዘመኑ ለ195 (ወይም በ2 ቅጂዎች ለ135) አመታት እንደ ቆየ ሲል ይህ ግን ትክክለኛ አይመስልም። ከአዋን (ኤላም) ነገሥታት ቀጥሎ ኪሽ ላዕላይነቱን እንደ ያዘ ይለናል። በኪሽ የነገሡ ንጉሦች 1) ሱሱዳ የሱፍ ጠራጊ፣ 2) ዳዳሲግ፣ 3) ማማጋል መርከበኛው፣ 4) ካልቡም የማማጋል ልጅ፣ 5) ቱጌ፣ 6) መን-ኑና የቱጌ ልጅ፣ 7)...(?) 8) ሉጋል-ጙ ናቸው ይለናል። ዳሩ ግን ለነዚህ ነገሥታት ሁሉ አንዳችም ሌላ ቅርስ ገና አልተገኘም። መጀመርያ 3 ስሞች የካልቡም ቅድመ-አባቶች ይሆናሉ፣ እንጂ ንጉሳዊ ስሞች አይመስሉም። ኪሽ በዚህ ወቅት ላዕላይነቱን ከያዘ ቅርስ ባለመገኘቱ ዘመኑ አጭር መሆን (ምናልባት 2274-2243 ዓክልበ. ግድም) አለበት። ከካልቡም በኋላ የተዘረዘሩ ስሞች በሱመር ላዕላይ ነገሥታት ሳይሆኑ ምናልባት የከተማው ከንቲቦች ብቻ ነበሩ። ከኪሽ በኋላ የሐማዚ ንጉሥ ሃዳኒሽ እንደ ተነሣ ዝርዝሩ ይጨምራል።

ከኪሽ 2ኛ ሥርወ መንግሥት ሁሉ የ1 ንጉሥ ስም ምናልባት በቅርስ ሊታይ ይችላል። በ1962 ዓ.ም. ሊቁ ቶርኪልድ ያቆብሰን እንደ መሰለው፣ በላጋሽ ንጉሥ ኤአናቱም «የአሞራዎች ጽላት» ላይ በአንድ ቦታ የኪሽ ንጉሥ በኤአናቱም ጦር ጫፍ ላይ ተቀርጾ ሲያሳይ ጽሕፈቱ ምናልባት «የኪሽ ንጉሥ ካልቡም» ይላል።[1]

  1. ^ Thorkild Jacobsen, Toward the image of Tammuz and other essays on Mesopotamian history and culture 1970, p. 393.
ቀዳሚው
የአዋን ንጉሥ
ሱመር (ኒፑር) አለቃ
2274-2243 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
ሐማዚ ንጉሥ ሀዳኒሽ
ቀዳሚው
ማማጋል፣ መርከበኛው
ኪሽ ንጉሥ
2274-2243 ዓክልበ. ግድም
ተከታይ
ቱጌ