ሞገድ ማለት በጊዜና በኅዋ ውስጥ የሚጓዝ ረብሻ ሲሆን አብላጫውን ጊዜ ይሄው ረብሻ የሚጓዘው ኃይልን ከአንድ ቦታ ወድ ሌላ ቦታ በማሻገር ነው። ሞገድ (ተንቀሳቃሽ ረብሻ) የሚያልፍበትን የቁስ አካል ሞለኪል በቋሚ ሁኔታ አቀማመጣቸውን አይቀይርም። ይልቁኑ እነዚህን ሞለኪሎች ባሉበት ቦታ በማርገብገብ በውስጣቸው ሰንጥቆ ያልፋል። ለምሳሌ ድምጽን ብንወስድ፣ በአየር ውስጥ ሲጓዝ የአየርን ጥቃቅን ክፍልፋዮች (ሞለኪሎች) አንዳቸው ባንዳቸው እንዲጋጩ በማድረግ ነው። ነገር ግን እነዚህ ሞለኪሎች ተጋጭተው በሄዱበት አይቀጥሉም። ይልቁኑ ከተጋጩ በኋላ በመፈናጠር ወደ ነበሩበት ይመለሳሉ። በዚህ አይነት መንገድ ሞገዱ ሰንጥቆ ሲያልፍ ነገር ግን አየሩ እነበረበት እንዳለ ይቀጥላል ማለት ነው። በሌላ ምሳሌ ለማየት የሳፋ (ጢሽት) ውሃ ላይ ቆርኪ ብናስቀምጥና ውሃው ላይ የውሃ ጠብታ ብናደርግ፣ ውሃው ገጽታ ላይ የምናየው ሞገድ ክብ እየሰራና እየሰፋ ወደ ሳፋው (ጢሽቱ) ዳር ቢሄድም፣ ቆርኪው ግን ሞገዱ ሲያልፈው ወደላይና ወደታች ከመዋዥቅ በቀር አብሮ ከሞገዱ ጋር ወደ ዳር አይሄድም። ባጠቃላይ መልኩ ማንኛውም በቁስ ውስጥ የሚያልፍ ሞገድ ኃይልን ከማስተላለፍ ውጭ በምንም አይነት መጠነ ይዘትን አያስተላልፍም። እኒህ በቁስ አካል ውስጥ የሚያልፉ ሞገዶች መካኒካል ሞገድ ይሰኛሉ።

የውሃ ግጽታ ላይ የሚንሸራሽር ሞገድ

ያለ ቁስ አካል መተላለፍ የሚችሉም ሞገዶች አሉ። ማለት ከመሬት ውጭ ባለው አየር በሌለበት ኅዋ ውስጥ የሚያልፉትን አይነት ማለት ነው። ከነዚህ ውስጥ ብርሃን አንዱ ነው፣ አለዚያ የፀሐይ ጨረር ከምድር አይደርስም ነበር።። ብርሃን እራሱ ኮረንቲና ማግኔት ማዕበል የተሰኙት የሞገድ ዝርያወች አባል ነው። ይህ ዝርያ እንግዲህ ኤክስ ሬይአንስታይ ቀይተባታይ ወይን ጠጅ የተባሉትን ሁሉ ይጠቀልላል። የሚንቀሳቀሱትም የኮሬንቲ እና ማግኔት ጠባያቸውን በቋሚ ጊዜ በማርገብገብ ነው። ሌላው እስካሁን ድረስ በቀጥታ ማስረጃ ያልተገኘለት የሥበት ሞገድ የተሰኘውም ምንም ቁስ በሌለበት ኅዋ ውስጥ እንደ ብራሃን እንዲጓጓዝ ይታመናል።