፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ ፩

የጳውሎስ መልዕክት


፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ በአዲስ ኪዳን ሁለተኛው መልዕክት ሲሆን ቅዱስ ጳውሎስ በቆሮንጦስ እያለ በ፶ ዎቹ ዓ.ም. ለቆሮንጦስ ሰዎች የጻፈው የመጀመሪያ መልዕክት ነው ። ፲፮ ምዕራፎች ይይዛል ። ይህ ፩ኛ ምዕራፍ ሲሆን በ፴፩ ንዑስ ክፍሎች ይከፈላል ።

፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ ፩
በ፫ኛው ክፍለ ዘመን የተጻፈ ፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ ፯:፴፫-፯ ፰:፬ በፓፒረስ ፲፭
አጭር መግለጫ
ፀሐፊ ጳውሎስ
የመጽሐፍ ዐርስት ፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ
የሚገኘው በአዲስ ኪዳን ፯ኛው መጽሐፍ
መደብ የጳውሎስ መልዕክት


ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንጦስ ሰዎች መልዕክት የጻፈበት ምክኒያት ብዙ ናቸው ለምሳሌ ትንሳዔ ሙታን የለም እስከማለት የደረሱ ነበሩ እንዲሁም በቆሮንቶስ ምዕመናን መሀከል ፣ እኔ የጳውሎስ ነኝ ፣ እኔ የአጵሎስ ነኝ ፣ የኢየሱስ ነኝ ...እያሉ መከፋፈላቸውን ሰምቶ ከዚህ ስህታቸው እንዲታረሙ ፤ በተጨማሪም ዓለምን ለማሳፈር እግዚአብሔር ታላቁን ሚሥጥር በዓለም በተናቁት ሰዎች እንዲገለፅ ማድረጉን ለማሳወቅ ጻፈው ።


ቆሮንጦስ
የቆሮንጦስ ወደብ መግቢያ
ግሪክ
፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ ፩ is located in ግሪክ
ቆሮንጦስ
ቅዱስ ጳውሎስ አብዛኛውን መልዕክቶቹን የጻፈበት ግሪክ የምትገኝ ጥንታዊት ከተማ ።


የሐዋርያው ጳውሎስ መልዕክት ፩ኛ ወደ ቆሮንጦስ ምዕራፍ ፩

ቁጥር ፩ - ፲ ለማስተካከል

1፤በእግዚአብሔር፡ፈቃድ፡የኢየሱስ፡ክርስቶስ፡ሐዋርያ፡ሊኾን፡የተጠራ፡ጳውሎስ፣ ወንድሙም፡ሶስቴንስ፥ 2፤በቆሮንቶስ፡ላለች፡ለእግዚአብሔር፡ቤተ፡ክርስቲያን፥በክርስቶስ፡ኢየሱስ፡ ለተቀደሱት፥ የእነርሱና፡የእኛ፡ ጌታ፡የኾነውን፡የጌታችንን፡የኢየሱስ፡ክርስቶስን፡ስም፡በየስፍራው፡ከሚጠሩት፡ዅሉ፡ ጋራ፡ቅዱሳን፡ለመኾን፡ ለተጠሩት፤ 3፤ከእግዚአብሔር፡ከአባታችን፡ከጌታም፡ከኢየሱስ፡ክርስቶስ፡ጸጋና፡ሰላም፡ለእናንተ፡ ይኹን። 4፤በክርስቶስ፡ኢየሱስ፡ስላመናችኹ፡በተሰጣችኹ፡በእግዚአብሔር፡ጸጋ፡ምክንያት፡ ዅልጊዜ፡ስለ፡እናንተ፡ አምላክን፡አመሰግናለኹ፤ 5-6፤ለክርስቶስ፡መመስከሬ፡በእናንተ፡ዘንድ፡እንደ፡ጸና፥በነገር፡ዅሉ፣በቃልም፡ ዅሉ፣በዕውቀትም፡ዅሉ፡ በርሱ፡ባለጠጋዎች፡እንድትኾኑ፡ተደርጋችዃልና። 7፤እንደዚህ፡የጌታችንን፡የኢየሱስ፡ክርስቶስን፡መገለጥ፡ስትጠባበቁ፡አንድ፡የጸጋ፡ ስጦታ፡እንኳ፡ አይጐድልባችኹም፤ 8፤ርሱም፡ደግሞ፡በጌታችን፡በኢየሱስ፡ክርስቶስ፡ቀን፡ያለነቀፋ፡እንድትኾኑ፡እስከ፡ ፍጻሜ፡ድረስ፡ ያጸናችዃል። 9፤ወደልጁ፡ወደጌታችን፡ወደኢየሱስ፡ክርስቶስ፡ኅብረት፡የጠራችኹ፡እግዚአብሔር፡ የታመነ፡ነው። 10፤ነገር፡ግን፥ወንድሞች፡ሆይ፥ዅላችኹ፡አንድ፡ንግግር፡እንድትናገሩ፡ባንድ፡ልብና፡ ባንድ፡ዐሳብም፡ የተባበራችኹ፡እንድትኾኑ፡እንጂ፡መለያየት፡በመካከላችኹ፡እንዳይኾን፡በጌታችን፡ በኢየሱስ፡ክርስቶስ፡ስም፡ እለምናችዃለኹ።

ቁጥር ፲፩ - ፳ ለማስተካከል

11፤ወንድሞቼ፡ሆይ፥በመካከላችኹ፡ክርክር፡እንዳለ፡ስለ፡እናንተ፡የቀሎዔ፡ቤተ፡ሰዎች፡ አስታውቀውኛልና። 12፤ይህንም፡እላለኹ፦እያንዳንዳችኹ፦እኔ፡የጳውሎስ፡ነኝ፥እኔስ፡የአጵሎስ፡ነኝ፥እኔ፡ ግን፡የኬፋ፡ነኝ፥እኔስ፡የክርስቶስ፡ነኝ፡ትላላችኹ። 13፤ክርስቶስ፡ተከፍሏልን፧ጳውሎስስ፡ስለ፡እናንተ፡ተሰቀለን፧ወይስ፡በጳውሎስ፡ስም፡ ተጠመቃችኹን፧ 14-15፤በስሜ፡እንደ፡ተጠመቃችኹ፡ማንም፡እንዳይል፡ከቀርስጶስና፡ከጋይዮስ፡በቀር፡ ከእናንተ፡አንድን፡እንኳ፡ስላላጠመቅኹ፡እግዚአብሔርን፡አመሰግናለኹ። 16፤የእስጢፋኖስንም፡ቤተ፡ሰዎች፡ደግሞ፡አጥምቄያለኹ፤ጨምሬ፡ሌላ፡አጥምቄ፡እንደ፡ ኾነ፡አላውቅም። 17፤ለማጥመቅ፡ክርስቶስ፡አልላከኝምና፥ወንጌልን፡ልሰብክ፡እንጂ፤የክርስቶስ፡መስቀል፡ ከንቱ፡እንዳይኾን፡በቃል፡ጥበብ፡አይደለም። 18፤የመስቀሉ፡ቃል፡ለሚጠፉት፡ሞኝነት፥ለእኛ፡ለምንድን፡ግን፡የእግዚአብሔር፡ ኀይል፡ነውና። 19፤የጥበበኛዎችን፡ጥበብ፡አጠፋለኹ፡የአስተዋዮችንም፡ማስተዋል፡እጥላለኹ፡ተብሎ፡ ተጽፏልና። 20፤ጥበበኛ፡የት፡አለ፧ጻፊስ፡የት፡አለ፧የዚች፡ዓለም፡መርማሪስ፡የት፡አለ፧እግዚአብሔር፡የዚችን፡ ዓለም፡ጥበብ፡ሞኝነት ፡ እንዲኾን፡አላደረገምን፧

ቁጥር ፳፩ - ፴፩ ለማስተካከል

21፤በእግዚአብሔር፡ጥበብ፡ምክንያት፡ዓለም፡እግዚአብሔርን፡በጥበቧ፡ስላላወቀች፥በስብከት፡ሞኝነት፡ የሚያምኑትን፡ሊያድን፡የእግዚአብሔር፡በጎ፡ፈቃድ፡ኾኗልና። 22፤መቼም፡አይሁድ፡ምልክትን፡ይለምናሉ፡የግሪክ፡ሰዎችም፡ጥበብን፡ይሻሉ፥ 23፤እኛ፡ግን፡የተሰቀለውን፡ክርስቶስን፡እንሰብካለን፤ይህም፡ለአይሁድ፡ማሰናከያ፡ለአሕዛብም፡ ሞኝነት፡ነው፥ 24፤ለተጠሩት፡ግን፥አይሁድ፡ቢኾኑ፡የግሪክ፡ሰዎችም፡ቢኾኑ፥የእግዚአብሔር፡ኀይልና፡ የእግዚአብሔር፡ጥበብ፡የኾነው፡ክርስቶስ፡ነው። 25፤ከሰው፡ይልቅ፡የእግዚአብሔር፡ሞኝነት፡ይጠበባልና፥የእግዚአብሔርም፡ድካም፡ከሰው፡ይልቅ፡ ይበረታልና። 26፤ወንድሞች፡ሆይ፥መጠራታችኹን፡ተመልከቱ፤እንደ፡ሰው፡ጥበብ፡ጥበበኛዎች፡የኾኑ፡ብዙዎች፥ ኀያላን፡የኾኑ፡ብዙዎች፥ባላባቶች፡የኾኑ፡ብዙዎች፡አልተጠሩም። 27፤ነገር፡ግን፥እግዚአብሔር፡ጥበበኛዎችን፡እንዲያሳፍር፡የዓለምን፡ሞኝ፡ነገር፡መረጠ፤ብርቱንም፡ነገር፡ እንዲያሳፍር፡እግዚአብሔር፡የዓለምን፡ደካማ፡ነገር፡መረጠ፤ 28፤እግዚአብሔርም፡የኾነውን፡ነገር፡እንዲያጠፋ፡የዓለምን፡ምናምንቴ፡ነገር፡የተናቀውንም፡ነገር፡ ያልኾነውንም፡ነገር፡መረጠ፥ 29፤ሥጋን፡የለበሰ፡ዅሉ፡በእግዚአብሔር፡ፊት፡እንዳይመካ። 30-31፤ነገር፡ግን፦የሚመካ፡በእግዚአብሔር፡ይመካ፡ተብሎ፡እንደተጻፈው፡ይኾን፡ዘንድ፥ከእግዚአብሔር፡ዘንድ፡ጥበብና፡ጽድቅ፣ቅድስናም፣ቤዛነትም፡በተደረገልን፡በክርስቶስ፡ኢየሱስ፡የኾናችኹ፡ከርሱ፡ነው።