አዳም ረታ ልቦለድግጥምአማርኛ የሚጽፍ ኢትዮጵያዊ ደራሲ ነው።

አዳም ረታ

ሕይወት ለማስተካከል

አዳም ረታ በ1950 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ተወለደ። በትምህርት አለም - በጂኦግራፊ የመጀመሪያ ዲግሪውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተቀብሏል። ሁለተኛ (የማስተርስ) ዲግሪውን ደግሞ በውጭ ሀገር አግኝቷል። የሚፅፈው በአብዛኛው ልቦለዶችን ቢሆንም ግጥሞችንም ይፅፋል። በተለያዩ ጊዜያት ግጥሞቹ በተለያዩ መፅሔቶች ላይ ታትመዋል። ያልታተሙ ግጥሞችም አሉት።[1]
ከተደራሲው ጋር የተዋወቀበት እና በኢትዮጵያ ስነ ጽሑፍ ተከታታዮችና አንባቢዎች ልብ ውስጥ የመሠረት ድንጋይ ያስቀመጠበት “አባ ደፋር እና ሌሎች አጫጭር ታሪኮች” በኩራዝ አሳታሚ ድርጅት የታተመው በ1977 ዓ.ም ነው። (በዚህ መድብል ውስጥ አራት ስራዎችን አዋጥቷል፡ “ድብድብ”፣ “ዕብዱ ሺበሺ”፣ “ሲሮኮ” እና “ሲፊንክስ”)[2]ሜጋ አሳታሚ ድርጅት1990 ዓ.ም ባሳተመው “ጭጋግና ጠል” የአጭር ታሪኮች ስብስብ “ዘላን” የተባለው ልቦለዱ ታትሟል። እነዚህ ሁለቱ ከሌሎች ደራሲዎች ስራዎች ጋር የታተሙለት ስለሆነ እንደ ወጥ ሳይቆጠሩ ነው ከላይ የሰፈረው የተባለው።

1981 ዓ.ም በኩራዝ አሳታሚ የታተመው “ማህሌት” የደራሲው የመጀመሪያ ወጥ የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ መፅሀፍ ነው። በሻማ ቡክስ1997 ዓ.ም የታተመው “ግራጫ ቃጭሎች” እንደ ብሉይ (classic) ሥራ ሊታይ የሚችልና የደራሲው ልዩ ብቃት የታየበት ወጥ ረጅም ልብወለድ ነው።
2001 ዓ.ም ሁለት ልዩ ስራዎች ይዞ የቀረበው አዳም፡ የአጫጭር ልብወለዶች ስብስብ የሆነው “አለንጋና ምስር” እና እርስ በርሳቸው በቀጭን የታሪክ ክር የሚገናኙ ልብወለዶች (ኖቬላዎች) ያካተተው “እቴሜቴ ሎሚ ሽታ” ለአንባቢያን አበርክቷል። ይህ የአጻጻፍ ስልቱ ሕጽናዊነት የሚባል ሲሆን ደራሲው በሌሎቹ መጻሕፍቱም ውስጥ በስፋት ተጠቅሞበታል፡፡

በቀጠሉት ሦስት ዓመታት በየዓመቱ አንዳንድ መፅሐፍ ለአንባቢያ ያደረሰ ሲሆን በ2002 ዓ.ም “ከሰማይ የወረደ ፍርፍር”፣ በ2003 ዓ.ም “ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ” እና በ2004 ዓ.ም “ሕማማት እና በገና” ታትመው ለንባብ በቅተዋል። “ከሰማይ የወረደ ፍርፍር” በተሰኘው መፅሀፉ ድንቅ የፋንታሲ (“ፈንጠዚያ”) ሥራዎች የተካተቱ ሲሆን በ”ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ” ለመጀመሪያ ጊዜ መቼቱን ከሀገር ውጭ በማድረግ የውጭውን ሕይወት በስሱ የዳሰሰ ሲሆን ከሌሎቹ ስራዎቹ በተለየ መልኩ ስለሀገራችን ፖለቲካ ወጣ-ገባ መንገድ በታዛቢ አይን ምልከታው፣ ትውስታውን … አስፍሯል፡፡ ሕማማትና በገና የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ ሲሆን ለየት ያለ ቅርፅ ያላቸው አንዳንድ ልቦለዶች ተካተውበታል።

ፍልስፍናውና ስልቱ ሕፅናዊነት በሚል ስያሜው ይፋ ሆኗል።



አዳም ረታ በተለየ የአፃፃፍ ስልቱ እና በስራዎቹ ጥልቀት በሃያስያን ዘንድ አዎንታዊ ሂስ እና ከፍተኛ አድናቆት ተችሮታል። ጥቂቱን ለመጥቀስ ያህል…

“…አዳም ረታ ታዋቂ ደራሲያን ከሆኑት ከሀዲስ አለማየሁበዓሉ ግርማዳኛቸው ወርቁፀጋይ ገብረመድህን… ጋራ መመደብ የሚችል ነው ሊባል ይችላል…” Aklilu Dessalegn
Adam Reta as a Literary Existentialist: Textual and Descriptive Criticism (2010)

…ዳኛቸው ወርቁ በ“አደፍርስ” የኢፒሶዲክ ሕግጋትን አጋምሶ ለማስተዋወቅ ከሞከረ ወዲህ በአማርኛ ሥነ-ጽሑፍ በኢፒሶዲክ ተሟልቶ የተገኘ ድርሰት “ግራጫ ቃጭሎች” ነው። … “ግራጫ ቃጭሎች” ከገፀ-ባህሪው አካልና ሥነ-ልቡና አሳሳል አልፈን ድንቅ ዓላማውን፣ ቋንቋውንና የሕይወት አተረጓጎሙን ስንመለከት የአዳም ረታ እውቀትና ልምድ ጠንከር - ጠጠር ብሎ በመዝገቡ በኩል ሲያስተጋባ ነው የምንመለከተው።…
ዓለማየሁ ገላጋይ -

ደራሲና ጋዜጠኛ
ኢሜጅ መጽሔት፣ ቅጽ 1፣ ቁጥር 02፣ ግንቦት 1998

ለሕትመት የበቁ የአዳም ረታ ስራዎች ለማስተካከል

  1. አባ ደፋር እና ሌሎች ታሪኮች - 1977 ዓ.ም (“ድብድብ”፣ “ዕብዱ ሺበሺ”፣ “ሲሮኮ” እና “ሲፊንክስ”)
  2. ማሕሌት - 1981 ዓ.ም
  3. ጭጋግና ጠል እና ሌሎች - 1990 ዓ.ም (ዘላን)
  4. ግራጫ ቃጭሎች - 1997 ዓ.ም
  5. አለንጋና ምስር - 2001 ዓ.
  6. እቴሜቴ ሎሚሽታ - 2001 ዓ.ም
  7. ከሰማይ የወረደ ፍርፍር - 2002 ዓ.ም
  8. ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ - 2003 ዓ.ም
  9. ሕማማትና በገና - 2004 ዓ.ም
  10. መረቅ - 2007 ዓ.ም
  11. የስንብት ቀለማት 2008 ዓ.ም
  12. አፍ 2010 ዓ.ም

ምንጮች ለማስተካከል

  1. ^ ጭጋግና ጠል ገፅ 108 አአ ሜጋ አሳታሚ ድርጅት 1990 ዓ.ም
  2. ^ አዲስ አድማስ ጋዜጣ

https://www.facebook.com/groups/

64220102416/

የውጭ ጠቋሚዎች ለማስተካከል

http://arefe.wordpress.com/2006/05/28/hello-world/#more-1