ዮጋ

ዮጋ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ብቻ ነውን?

በዛሬው ጊዜ ሰዎች ሸንቃጣ ሆነው ለመታየትና ጥሩ ጤንነት ለማግኘት በእጅጉ ይመኛሉ። ይህም ብዙዎች ጅምናዝየሞችንና የጤና ክበባትን እንዲያዘወትሩ አድርጓቸዋል። በምዕራቡ ዓለም የሚኖሩ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ለዚሁ ሲሉ በምሥራቁ ዓለም የሚኖሩ ሰዎች ወደሚያዘወትሩት የዮጋ እንቅስቃሴ ፊታቸውን አዙረዋል። በተጨማሪም በውጥረት፣ በመንፈስ ጭንቀትና በተስፋ መቁረጥ የሚሰቃዩ ሰዎች እፎይታና መፍትሔ ለማግኘት ዮጋ መሥራት ጀምረዋል። በተለይ የሂፒዎች ዘመን ተብሎ ከሚታወቀው ከ1960ዎቹ ዓመታት ወዲህ የምሥራቁ ዓለም ሃይማኖቶችና ምስጢራዊ ሥርዓቶቻቸው በምዕራቡ ዓለም በእጅጉ ተስፋፍተዋል። የዮጋ የማሰላሰል ሥርዓት በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅ እንዲሆን ያደረጉት የፊልም ኮከቦችና የሮክ ሙዚቃ አቀንቃኞች ናቸው። ዮጋ በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅነት እያገኘ መምጣቱን ስናይ የሚከተሉትን ጥያቄዎች እናነሳ ይሆናል:- ‘ዮጋ ጤናማና ሸንቃጣ ሰውነት እንዲሁም የአእምሮ ሰላም የሚያስገኝ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ብቻ ነውን? ዮጋ ምንም ዓይነት ሃይማኖታዊ ንክኪ የለውምን? ዮጋ በክርስቲያኖች ዘንድ ተቀባይነት ሊኖረው ይችላልን?’ የዮጋ ታሪክ “ዮጋ” የሚለው ቃል ቀንበር የሚል ትርጉም ካለው የእንግሊዝኛ ቃል ጋር ዝምድና አለው። ማጣመር ወይም ማጣመድ፣ ቀንበር መጫን ወይም መቆጣጠር የሚል ፍቺ ሊሰጠው ይችላል። ለአንድ የሒንዱ እምነት ተከታይ ዮጋ ማለት ከሰው በላይ ከሆነ ኃይል ወይም ከመንፈሳዊ አካል ጋር ውህደት ለመፍጠር ሰውነትን ለመግራት ወይም ለማሰልጠን የሚረዳ ዘዴ ነው። “የአካልን፣ የአእምሮንና የነፍስን ኃይል ማቆራኘት” ተብሎም ሊገለጽ ይችላል። ዮጋ የጀመረው መቼ ነው? በዛሬዋ ፓኪስታን በኢንደስ ሸለቆ ውስጥ በተለያየ የዮጋ የአቀማመጥ ሥርዓት የተቀመጡ ሰዎች የተቀረጹባቸው ማኅተሞች ተገኝተዋል። አርኪኦሎጂስቶች የኢንደስ ሸለቆ አካባቢ ከፍተኛ የሥልጣኔ ደረጃ ላይ ደርሶ የነበረው ከሦስተኛው እስከ ሁለተኛው መቶ ዘመን ከዘአበ ባለው ጊዜ ውስጥ እንደሆነ ይናገራሉ። ይህ ጊዜ ደግሞ የሜሶጶጣሚያ ባሕል ከገነነበት ጊዜ ጋር በጣም የሚቀራረብ ነው። ከእነዚህ ሁለት ቦታዎች በተገኙ የእጅ ጥበብ ሥራዎች ላይ አንድን አምላክ የሚወክል አንድ ሰው ከእንስሳት ቀንድ የተሠራ አክሊል አድርጎና በእንስሳት መካከል ቆሞ የሚታይ ሲሆን ምስሉ ‘በኃያል አዳኝነቱ’ የሚታወቀውን ናምሩድን የሚያስታውስ ነው። (ዘፍጥረት 10:8, 9) የሂንዱ እምነት ተከታዮች የዮጋ አቀማመጥ ያላቸው ምስሎች የእንስሳትና የዮጋ ጌታ የሆነው ሲቫ የተባለው አምላክ መለያዎች እንደሆኑ ይናገራሉ። ብዙውን ጊዜ ለሲቫ ለሚቀርበው አምልኮ የሚያገለግለው ሐውልት በወንድ ብልት አምሳል የተሠራ ነው። ስለሆነም ሂንዱ ዎርልድ የተባለው መጽሐፍ ስለ ዮጋ ሲናገር “ዮጋ በአብዛኛው ከአርያን ዘመን በፊት ይሠራባቸው የነበሩትን ብዙ ጥንታዊ አስተሳሰቦችና ራስን የመገሰጽ ልማድ ያካተተ ሥርዓት ነው” ይላል። ቀደም ሲል የዮጋ ሥርዓት ከትውልድ ወደ ትውልድ ይተላለፍ የነበረው በቃል ነበር። ከጊዜ በኋላ ግን ህንዳዊው የዮጋ ጠቢብ ፐቶንጀሊ ዮጋ ሱትራ በሚል ስያሜ ሥርዓቶቹን አንድ በአንድ በመጽሐፍ አስፍሯቸዋል። ይህ መጽሐፍ የዮጋ ዋነኛ መመሪያ ሆኖ ያገለግላል። ፐቶንጀሊ፣ ዮጋ “የሰውን ልጅ ተፈጥሮ ማለትም አካላዊና አእምሮአዊ ክፍሎችን በመግራት ፍጽምናን ለማግኘት ጥረት የሚደረግበት ዘዴ” እንደሆነ ተናግረዋል። ዮጋ ከጅምሩ አንስቶ እስከአሁን ድረስ የምሥራቁ ዓለም ሃይማኖቶች በተለይ ደግሞ አሁን የሂንዱ፣ የጃይኒዝምና የቡዲዝም እምነቶች አብይ ክፍል ሆኖ ቆይቷል። አንዳንድ ሰዎች ዮጋ በየትኛውም ሥፍራ ሰፍኖ ከሚገኘው መንፈስ ጋር ውህደት እንዲፈጥሩ በማድረግ ሞክሻ ወይም ነጻነት እንደሚያጎናጽፋቸው ይሰማቸዋል። ስለሆነም ቀደም ሲል ያነሳነውን ጥያቄ ደግመን እናነሳለን:- ‘ዮጋ ከሃይማኖት ጋር ምንም ንክኪ የሌለው ጤናን ለመጠበቅና አእምሮን ለማዝናናት የሚሠራ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ብቻ ነውን?’ አመጣጡን ስንመለከት መልሳችን አይደለም የሚል ነው። የዮጋ መጨረሻ ውጤት ምንድን ነው? የዮጋ እንቅስቃሴ ዓላማ አንድን ግለሰብ ሰውነቱን በመግራት ከሰው በላይ ከሆነ መንፈስ ጋር “ጥምረት” ወይም ውህደት እንዲፈጥር ማድረግ ነው። ታዲያ ይህ መንፈስ ምንድን ነው? ቤንጃሚን ዎከር የተባሉት ደራሲ ሂንዱ ዎርልድ በተባለው መጽሐፍ ላይ እንደሚከተለው ሲሉ ጽፈዋል:- “ዮጋ የጥንቆላ ድርጊቶች አንድ ብለው የሚጀምሩበት ደረጃ ሲሆን የቃሉ ትርጉምም አስማትንና ሟርትን እንደሚጨምር ያሳያል” በማለት ተናግረዋል። የሂንዱ ፈላስፎች ምንም እንኳ አንድ ሰው ዮጋ የሚሠራበት ዋነኛ ዓላማ ይህ አይደለም ብለው ቢናገሩም ዮጋ ከሰብዓዊ ተፈጥሮ ውጪ የሆነ ኃይል እንደሚያጎናጽፍ ያምናሉ። ለምሳሌ ያህል የቀድሞ የህንድ ፕሬዚዳንት የነበሩት ዶክተር ኤስ ራዳክሪሽናን ኢንዲያን ፊሎሶፊ በተባለው መጽሐፍ ላይ ዮጋ ስለሚሠራ ሰው ሲናገሩ እንዲህ ብለዋል:- “በተለያዩ መንገዶች አማካኝነት ሰውነትን በመግራት ኃይለኛ ሙቀትንና ቅዝቃዜን መቋቋም የሚቻልበት ደረጃ ላይ መድረስ ይቻላል። . . . ዮጋ የሚሠራው ሰው በርቀት ያለን ነገር መመልከትና ከሩቅ ቦታ ድምፅ መስማት ይችላል። . . . የተለያየ ቦታ ያሉ ሁለት ግለሰቦች የተለመዱትን የመገናኛ ዘዴዎች መጠቀም ሳያስፈልጋቸው የሐሳብ ግንኙነት ማድረግ ይችላሉ። . . . ዮጋ የሚሠራው ሰው አካሉን መሰወር ይችላል።” ዮጋ የሚሠራ አንድ ሰው በሾሉ ምስማሮች ላይ መተኛት ወይም በፍም ላይ መሄድ ይችላል ሲባሉ አንዳንዶች ምትሃት እንደሆነ ይሰማቸዋል ሌሎች ደግሞ ሊታመን የማይችል እንደሆነ አድርገው ይቆጥሩታል። ሆኖም ህንድ ውስጥ እነዚህ የተለመዱ ክስተቶች ናቸው። ከዚህም በተጨማሪ ለሰዓታት ፀሐይን ፍጥጥ ብሎ እየተመለከቱ በአንድ እግር ቀጥ ብሎ መቆም እንዲሁም ትንፋሽን ውጦ ለረዥም ሰዓት በአሸዋ ውስጥ ተቀብሮ መቆየት የተለመዱ ድርጊቶች ናቸው። ዘ ታይምስ ኦቭ ኢንዲያ በሰኔ 1995 እትሙ ላይ አንዲት የሦስት ዓመት ከስድስት ወር ልጅ በጀርባዋ ተንጋላ ተመስጣ በማሰላሰል ላይ እያለች 750 ኪሎ ግራም የሚመዝን ክብደት ያለው መኪና በሆዷ ላይ እንዲሄድ መደረጉን ዘግቧል። ልጅቷ አንዳችም ጉዳት ሳይደርስባት ተነስታ ስትሄድ በዚያ የነበሩት ሰዎች በጣም ተገርመዋል። ሪፖርቱ አክሎ “ይህ ዮጋ ምን ያህል ኃይል እንዳለው የሚያሳይ ነው” ብሏል። አንድ ሰው በራሱ እነዚህን እንግዳ ክስተቶች መፈጸም እንደማይችል የታወቀ ነው። ስለሆነም አንድ ክርስቲያን እንዲህ እያለ ራሱን መጠየቅ ይኖርበታል:- እነዚህ ድርጊቶች ምን የሚጠቁሙት ነገር አለ? ‘በምድር ሁሉ ላይ ብቻውን ልዑል’ በሆነው በይሖዋ አምላክ እርዳታ የሚከናወኑ ድርጊቶች ናቸው ወይስ በሌላ? (መዝሙር 83:18) መጽሐፍ ቅዱስ ለእነዚህ ጥያቄዎች የማያሻማ መልስ ይሰጣል። እስራኤላውያን ከነዓናውያን ወደሚኖሩበት ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመግባት ተቃርበው በነበረበት ጊዜ ይሖዋ በሙሴ በኩል ለእስራኤል ልጆች “እነዚያ አሕዛብ የሚያደርጉትን ርኩሰት ታደርግ ዘንድ አትማር” ብሏቸው ነበር። “ርኩሰት” የተባሉት ነገሮች ምንድን ናቸው? ሙሴ ‘ከምዋርት፣ ከአስማትና ከመተት’ እንዲርቁ አስጠንቅቋል። (ዘዳግም 18:9, 10) እነዚህ ድርጊቶች የአጋንንትና የሥጋ ሥራዎች በመሆናቸው በአምላክ ፊት እንደ ርኩስ ይታያሉ።—ገላትያ 5:19-21 ለክርስቲያኖች የተተወ ምርጫ አይደለም ሰዎች ይህን ሐሳብ ይቀበሉትም አይቀበሉት ዮጋ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ብቻ አይደለም። ሂንዱ ማነርስ፣ ካስተምስ ኤንድ ሴሪሞኒስ የተባለው መጽሐፍ በአንድ የሂንዱ መንፈሳዊ መሪ የሚሠለጥኑ ሁለት የዮጋ ተማሪዎችን ገጠመኝ አስፍሯል። አንደኛው እንዲህ ይላል:- “ያለ የሌለ ኃይሌን ተጠቅሜ ትንፋሼን ውጬ ለመቆየት ጥረት አደርግና ራሴን ወደ መሳት ስደርስ እተነፍሳለሁ። . . . አንድ ቀን ቀትር ላይ እየተንዠዋዠወች የምትጓዝ ደማቅ ጨረቃ ያየሁ መሰለኝ። በሌላ ጊዜ ደግሞ እኩለ ቀን ላይ ድቅድቅ ባለ ጨለማ ውስጥ እንዳለሁ ሆኖ ተሰማኝ። ሁኔታውን ለአስተማሪዬ . . . ስነግረው በጣም ነበር የተደሰተው። . . . ጥረቴን በቀጠልኩ መጠን በቅርቡ ከዚህም የበለጠ አስደናቂ ነገር እንደሚያጋጥመኝ በመግለጽ አበረታታኝ።” ሁለተኛው ሰው እንዲህ በማለት ተናግሯል:- “በየዕለቱ ዓይኔን ሳላርገበግብና ካለሁበት ቦታ ንቅንቅ ሳልል ወደ ሰማይ ፍጥጥ ብዬ እንድመለከት አዘዘኝ። . . . አንዳንድ ጊዜ በአየሩ ውስጥ የእሳት ብልጭታ ያየሁ ይመስለኛል። አንዳንዴ ደግሞ እንደ እሳት የሚንቀለቀሉ ፕላኔቶችንና ሌሎች ከዋክብትን ያየሁ ይመስለኛል። ይህን ማየት በመቻሌ አስተማሪዬ በጣም ተደስቷል።” የሂንዱ እምነት ሃይማኖታዊ አስተማሪዎች እነዚህ እንግዳ የሆኑ ክስተቶች የዮጋ እንቅስቃሴ ዓይነተኛ ግብ ላይ ለመድረስ በሚደረገው ጉዞ የሚገኙ ውጤቶች ናቸው ብለው ያስባሉ። የዮጋ የመጨረሻው ግብ የራሱ ስብዕና ከሌለው ታላቅ መንፈሳዊ አካል ጋር አንድ መሆን ነው። ይህንንም ሞክሻ ብለው ይጠሩታል። ይህ ደረጃ “ሆነ ብሎ አእምሮ ማሰቡን እንዲያቆም ማድረግ” ተብሎም ሊገለጽ ይችላል። ይህ ደግሞ ክርስቲያኖች ሊኖራቸው ከሚገባው ዓላማ ጋር የሚጋጭ ነው። ክርስቲያኖች እንዲህ የሚል ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል:- “ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኋለሁ፣ እርሱም ለአእምሮ የሚመች [“በማመዛዘን ችሎታችሁ ተጠቅማችሁ የምታቀርቡት፣” NW ] አገልግሎታችሁ ነው። የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ።”—ሮሜ 12:1, 2 የተሻለውን የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መምረጥ ለእያንዳንዱ ግለሰብ የተተወ ነው። ይሁን እንጂ ክርስቲያኖች ስፖርታዊ እንቅስቃሴም ይሁን መብል፣ መጠጥ፣ ልብስ፣ መዝናኛ ወይም ማንኛውም ሌላ ነገር ከይሖዋ አምላክ ጋር የመሠረቱትን ወዳጅነት እንዲያበላሽባቸው አይፈቅዱም። (1 ቆሮንቶስ 10:31) ለጤንነታቸው በማሰብ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ የሚፈልጉ ክርስቲያኖች አደገኛ ከሆነው የመናፍስትነት ድርጊትና ከአስማት ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸው የተለያዩ የስፖርት ዓይነቶችን መርጠው መሥራት ይችላሉ። ከሐሰት ሃይማኖት የመጡ ልማዶችንና እምነቶችን ከመከተል በመቆጠብ አምላክ በአካልም ሆነ በአእምሮ ዘላቂነት ያለው ፍጹም ጤንነት የምናገኝበትን ጽድቅ የሰፈነበት አዲስ ሥርዓት የሚያመጣልንን ጊዜ በጉጉት እንጠብቅ።—2 ጴጥሮስ 3:13፤ ራእይ 21:3, 4 [በገጽ 22 ላይ የሚገኝ ሥዕል] ብዙዎች ከመናፍስታዊ ድርጊቶች ጋር ምንም ዓይነት ንክኪ በሌላቸው ጤናማ እንቅስቃሴዎች ይካፈላሉ።

በመሳፍንት ተክለፃድቅ