አቡነ ጴጥሮስ

የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የአርበኝነት ታሪክ


ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ቤተክርስቲያን በአደራነት የሰጠቻቸውን ኃላፊነት ለመወጣት ሕዝበ ክርስቲያኑን በጸሎታቸው እየደገፉ በትምህርታቸው እያበረቱ በማስተዳደር ላይ እንዳሉ በ፲፱፳፰ ዓ.ም. አረመኔው የኢጣልያ ፋሺስት በግፍ ሀገራችንን ለመውረር ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት በማለት ባሕርን አቋርጦ መጣ ፡፡ አጭር የጀግንነት ታሪካቸውን ዝቅ ብለው ቪዲዮ ክሊፕ ላይ ማዳመጥ ይችላሉ ።

አቡነ ጴጥሮስ
እውነተኛ ጳጳስ
የኢትጵያ ጳጳስ ፣ በፋሺስቶች ተገድለው ሰማዕት የሆኑ
የኢትጵያ ጳጳስ ፣ በፋሺስቶች ተገድለው ሰማዕት የሆኑ
ቅዱስ ጅግና ሰማዕት
ስም በመጀመሪያ "መገርሳ በዳሳ"
በኋላ "መምህር ኃይለማርያም"
መጨረሻ "አቡነ ጴጥሮስ"
የተወለዱት ፲፰፸፭ ዓ.ም.
የትውልድ ቦታ ኪንዶ ኮይሻ (ወላይታ)
ያረፉበት ቀን ሐምሌ ፳፰ ፲፱፳፰ ዓ.ም. በሰማዕትነት
የሚከበሩት በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ


ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሀገር በመጣ ወራሪ ቀጥተኛ ተጠቂናትና ሊቃውንቷ፣ ገዳማትና አድባራቷ እንዲሁም ንዋያተ ቅድሳቷ በወራሪው የኢጣልያ ኃይል ይጨፈጨፉና ይቃጠሉ ገቡ ፡፡ ይህ ግፍ በዕውቀት ኮትኩታ ባሳደገቻቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ሲፈጸም ያዩት ብፁዕነታቸው ወራሪውን ኃይል ከኢትዮጵያውያኑ አርበኞች ጋር በመሆን በጸሎት ሊዋጉት ወሰኑ ፡፡

የብፁእ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ አጭር የጀግንነት ታሪክ አድናቆት ለድሬቲዩብ

በመጀመሪያ የወቅቱ የሀገሪቱ መሪ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል ከአረመኔው ፋሺስት ጦር ጋር በመፋለም ላይ የነበረውን አርበኛ ለማበረታታት ወደ ማይጨው በሔዱ ጊዜ ብፁዕነታቸው ተከትለው ሔዱ፡፡ ይሁን እንጂ ንጉሡም ሆኑ ብፁዕነታቸው ከሠራዊቱ ጋር ተቀላቅለው ብዙም ሳይቆዩ የጠላት ጦር በመርዝ የታገዘ ጥቃት በስፋት በመክፈቱ የኢትዮጵያ ሠራዊተ ወደ ኋላ እንዲያፈገፍግ ሆነ፡፡ በዚህም የተነሣ ንጉሡ ወደ አዲስ አበባ ሲመለሱ ብፁዕነታቸውም አብረው ተመለሱ ፡፡ እዚሁ እሞታለሁ ብለው እንቢ ያሉት ንጉሡ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ከሌሎች አባቶች ጋር ብፁዕነታቸው ያደረጉት ሚና ቀላል እንዳልነበር ይነገራል ፡፡ በበለጠ ለመረዳት ይህን ይመልከቱ

ቆራጥ ውሳኔያቸው ለማስተካከል

ይሁን እንጂ በጠላት የግፍ ጥቃት ክፉኛ ያዘኑት ብፁዕነታቸው በአዲስ አበባ ለመቀመጥ አልፈቀዱም፡፡ በታላቁ የደብረ ሊባኖስ ገዳም ተሰባስበው የቤተ ክርስቲያን አምላክ እግዚአብሔር በኢትዮጵያውያን ላይ የመጣውን ችግር እንዲያስታግስ በጸሎት እየለመኑ ወደ ነበሩት አባቶችና አርበኞች በመሄድ ለሀገርና ለነጻነት መሞት ቅዱስ ተግባር መሆኑን በመስበክ ሁሉም እንዲጋደሉ ማሳሰብ እና ማትጋት ጀመሩ፡፡ ምንም እንኳን ድልን ባይቀዳጅም በእርሳቸው ስብከት የተነሣሡት አርበኞችም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ጠላትን ወግተዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ብፁዕነታቸውም አብረው ነበሩ፡፡

 
ጅግናው ጳጳስ አቡነ ጴጥሮስ

ያጋጠማቸው እክል ለማስተካከል

ብፁዕነታቸው የነበሩበት የአርበኞች ጦር ወደ አዲስ አበባ ቢመጣም ድል ላለመቀዳጀቱ ምክንያቱ የመረጃ ልውውጥ ክፍተት እንደነበር ይነገራል፡፡ ይኸውም “የሰላሌ አርበኞች” ተብሎ የሚታወቀው፣ በነደጃዝማች አበራ ካሣ ይመራ የነበረውና በደብረ ሊባኖስ ጫካዎች ውስጥ መሽጎ የነበረው አርበኛ ጦር በሸንኮራ በኩል ከነበረውና በደጃዝማች ፍቅረ ማርያም ይመራ ከነበረው አርበኛ ጦር፣ በምዕራብ በኩል ከነበረውና በደጃዝማች ባልቻ አባ ነፍሶ ይመራ ከነበረው አርበኛ ጦር ጋር በአንድ ጊዜ ተንቀሳቅሶ አዲስ አበባ ላይ ወንበሩን አደላድሎ የተቀመጠውን የግራዚያኒን ጦር ሊወጋ ይነጋገራል፡፡ ይሁን እንጂ በስምምነቱ መሠረት ሦስቱም የጦር ኃይል ምታ ነጋሪት ክተት ሠራዊት ብሎ ወደ አዲስ አበባ ቢንቀሳቀስም በሦስቱም አቅጣጫ በአንድ ጊዜ ባለ መድረሱ በጠላት ላይ ያደረሰው ጉዳት ቀላል የሚባል ባይሆንም በተናጠል እየተመታ ወደ መጣበት ተመለሰ፡፡ በመጀመሪያ በኮተቤ በኩል የደረሰው የደጃዝማች ፍቅረ ማርያም ጦር ነበር፡፡ ይህ ጦር የካ ሚካኤል ላይ ሲደርስ ተመትቶ ተመለሰ፡፡ የጠላት ጦር የደጃዝማች ፍቅረ ማርያምን ጦር ወደ መጣበት መልሶ ወደ አዲስ አበባ ሲመለስ የደጃዝማች ባልቻ ጦር በባቡር ጣቢያ በኩል መጣሁ አለ፡፡ እሱንም መትቶ መለሰ፡፡ በመጨረሻ ደግሞ የደጃዝማች አበራ ጦር በእንጦጦ በኩል አድርጎ መጣ ፡፡ እሱም በጠላት ጦር ተመትቶ ተመለሰ ፡፡

የመጨረሻ ውሳኔያቸው ለማስተካከል

በዚህ ዓይነት ሦስቱም ኃይሎች በአንድ ጊዜ ባለማጥቃታቸው ወደየመጡበት ሲመለሱ ከሰላሌ አርበኞች ጋር የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ጠላት ከኢትዮጵያውያኑ ነጥቆ አገሬ ከተማዬ ብሎ በመቀመጥ በመላ ሀገሪቱ የሚያካሒደውን ጭፍጨፋ የሚመራባትንና ትእዛዝ የሚያስተላልፍባትን ከተማ አዲስ አበባን ትተው ለመሄድ አልፈቀዱም፡፡ በመሆኑም “ብችል በኢትዮጵያውያን ላይ እያደረሰ ያለውን ግፍ በቅርብ ርቀት ሆኖ የሚመለከተውን ሕዝብ በማትጋት በጠላት ላይ እንዲነሳ አደርጋለሁ፤ ካልሆነ ደግሞ እዚሁ እሞታለሁ” ብለው ከአርበኞች ተነጥለው በአዲስ አበባ ቀሩ፡፡

ሰማዕቱ ጴጥሮስ ለማስተካከል

ይሁን እንጂ ጠላት በመላ ከተማዋ ባሰማራቸው በርካታ ባንዳዎች መካከል ብፁዕነታቸው እንዳሰቡት ሊንቀሳቀሱ አልቻሉም፡፡ በመጨረሻ እዚሁ ከተማ ተሰውሬ መኖር አልፈልግም፤ ወደ ገጠር ፊቴን አልመልስም በማለት ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም በወቅቱ የኢጣሊያ እንደራሴ ለነበሩት ራስ ኃይሉ እጃቸውን ሰጡ፡፡ እራስ ኃይሉም ወዲያውኑ ለግራዚያኒ አሳልፈው ሰጧቸው፡፡

ብፁዕነታቸው በተጠቀሰው ቀን እጃቸውን ከሰጡበት ጊዜ ጀምሮ በጠላት የጥይት እሩምታ በሰማዕትነት እስካለፉበት ጊዜ ድረስ የነበረውን ሂደት ኮርየሬ ዴላሴራ የተባለው የጋዜጣ ወኪል እና የምስራቅ አፍሪካ ዜና መዋዕለ አዘጋጅ የነበረው ፓጃሌ የተባለ ጋዜጠኛ እ.ኤ.አ ሰኔ 15 ቀን 1936 ዓ.ም አዲስ አበባ በነበረ ጊዜ በብፁዕነታቸው የተሰጠውን ፍርድና የተፈፀመውን ግድያ ባየው እና በተመለከተው መንገድ እንደሚከተለው ጽፎ ነበር፡

ሐምሌ 22 ቀን 1928 አቡነ ጴጥሮስ ተይዘው ወደ ግራዚያኒ ቀረቡ ፡፡ በዚህ ጊዜ አቡነ ቄርሎስ የተባሉት “ግብፃዊ ጳጳስ ቀርበው ለእስክንድሪያው መንበረ ፓትርያርክ ምክር ቤት ሳታሰማ በአቡነ ጴጥሮስ ላይ አንዳች ነገር ማድረግ አይገባህም” ሲሉ ለግራዚያኒ ነገሩት ፡፡ ምክንያቱም ይላሉ አቡነ ቄርሎስ “አቡነ ጴጥሮስ ታላቅ ሰው ናቸው፡፡ በመሰረቱ ሊያዙ ባልተገባ ነበር፡፡ ከተያዙ ደግሞ ልትገላቸው ትችላለህ፡፡ ነገር ግን በእርሳቸው ላይ የምታደርገውን ነገር ሁሉ ለእስክንድሪያው መንበረ ፓትርያርክ ምክር ቤት ሳታሰማ ምንም ማድረግ አይገባህም” አሉት፡፡

አቡነ ቄርሎስ ይህን ማለታቸው በዲፕሎማቲክ ደረጃ ለዓለም ለማሰማት እና የአቡነ ጴጥሮስን ህይወት ለማትረፍ አስበው እንደነበር ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን ግራዚያኒ ይህ የአቡነ ጴጥሮስ የሞት ፍርድ እንኳንስ እስከ ግብፅ ከአዲስ አበባ ውጪ እንኳን ከመሰማቱ በፊት በግማሽ ቀን እንዲፈፀም ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ በእርግጥ ምንም እንኳን ከመገደል ባያመልጡም ብፁዕነታቸው እንደተያዙ ንቡረ ዕድ ተክለሀይማኖት/አዲስ ተክሌ/ና ሌሎች ሊቃውንት ወደ አቡነ ጴጥሮስ ዘንድ በመሄድ ማልደዋቸው ነበር ይባላል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ቁመታቸው ረዘም፣ ፊታቸው ዘለግ ያለ፣ መልካቸው ጠየም ያለ፣ አዋቂነታቸው እና ትህትናቸው ከገፃቸው የሚነበብ ሲሆን በዚህ ጊዜ ለብሰውት የነበረው ልብስ ጵጵስና ጥቁር ካባ ያውም በጭቃ የተበከለ ነበር ፡፡

 

በዚህ ሁኔታ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ወደ ችሎት ቀረቡ፡፡ ለፍርድም የተሰየሙት ዳኞች ሦስት ሲሆኑ እነዚህም የጣሊያኖች የጦር ሹማምንት ናቸው፡፡ የመካከለኛው ዳኛ ኮሎኔል ነበር፡፡ የቀረበባቸውም ወንጀል ሕዝብ ቀስቅሰዋል፣ እራስዎም ዐምፀዋል፣ ሌሎችንም እንዲያምፁ አድርገዋል የሚል ነበር፡፡ ዳኛውም “ካህናቱም ሆኑ የቤተ-ክህነት ባለሥልጣኖች ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ቄርሎስም የኢጣሊያንን መንግሥት ገዢነት አምነው አሜን ብለው ሲቀበሉ እርስዎ ለምን ዐመፁ? ለምን ብቻዋን አፈንጋጭ ሆኑ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡

አቡነ ጴጥሮስም የሚከተለውን መለሱ፡፡ “አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ናቸው፤ ስለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን የሚገዳቸው ነገር የለም፡፡ እኔ ግን ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ ሐላፊነትም ያለብኝ የቤተ ክርስቲያን አባት ነኝ፡፡ ስለዚህ ስለ ሀገሬና ስለ ቤተክርስቲያኔ እቆረቆራለሁ፡፡ ከዚህ በቀር ለእናንተ ችሎት የማቀርበው ነገር የለኝም፡፡ ለፈጣሪዬ ብቻ የምናገረውን እናገራለሁ፡፡ እኔን ለመግደል እንደወሰናችሁ ዐውቃለሁ፡፡ ስለዚህ በእኔ ላይ የፈለጋችሁትን አድርጉ፡፡ ግን ተከታዮቼን አትንኩ” አሉ፡፡

“ይህንንም ብለው በጥይት ተደብድበው ሲገደሉ እንዲያይ ተጋብዞ ለተሰበሰበው ሕዝብ የሚከተለውን ሕያው መልእክት አስተላለፉ “አረማዊ የሆነው የፋሺስት መንግሥት ቤተ-ክርስቲያንን ለማቃጠል፣ ሕዝበ ክርስቲያንን ለመግደል፣ ሃይማኖትን ለማጥፋት፣ ታሪካችንን ለማበላሸት የመጣ ነው እንጂ በጎ ለመሥራት እውነተኛ ፍርድ ለመስጠት ስላልመጣ ለዚህ ለግፈኛ አትገዙ፡፡ ስለ ውድ ሀገራችሁ፣ ስለ ቀናች ሃይማኖታችሁ ተከላከሉ፡፡ ነፃነታችሁ ከሚረክስ ሙታችሁ ስማችሁ ቢቀደስ ታላቅ ዋጋ ያለው ክብር ታገኛላችሁ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዚህ ለጠላት እንዳይገዛ አውግዣለሁ፤ የኢትዮጵያ መሬት ጠላትን ብትቀበል የተረገመች ትሁን፡፡ በፈጣሪዬ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተገዘተች ትሁን፡፡”

ጋዜጠኛው ይቀጥላል፡፡

“እኒህ ጳጳስ ሐቀኛ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ለኢጣሊያ ለጋስዮን ታዝዞ የመጣው አስተርጓሚ ዳኞች የሚሉትን ብቻ ከማስተርጎም በቀር ጳጳሱ የሚናገሩትን ሐቀኛ ንግግር አላስተረጎመም፡፡ እኔ እንኳን የሰማሁት በአዲስ አበባ ለሠላሳ ዓመት የኖረው የእቴጌ ሆቴል ሐላፊ የነበረው የግሪክ ዜጋ ማንድራኮስ አጠገቤ ተቀምጦ ስለ ነበር የተናገሩትን ሁሉ ስለ ገለጠልኝ ነው፡፡ እኔ እንደ ሰማሁት ፍርዱን ለመስማት በብዛት የተሰበሰቡት ጣሊያኖችና ታዝዞ የወጣው የአዲስ አበባ ሕዝብ ሐቀኛ የሆነውን ንግግራቸውን ቢሰሙ ኖሮ ልባቸው ይነካ ነበር” ይላል፡፡

ሆኖም አስተርጓሚው በጳጳሱ ላይ ተፅዕኖ ስላሳደረባቸው እውነተኛ ንግግራቸው ሳይገለጥ ቀረ፡፡ ቀጥሎም ብፁዕነታቸው በፍርድ ችሎት ላይ እንዳሉ ሕዝቡ ሁሉ ስለ ርሳቸው እያዘነ ሳለ መስቀላቸውን አውጥተው እየፀለዩ ሕዝቡን ባረኩ ፡፡ ወዲያው የሞታቸው ፍርድ ሲሰማ ሕዝቡ በኢጣልያ የእጅ ሰላምታ ዓይነት እጁን እንዲያነሳ ታዘዘ ፡፡ በዚያን ጊዜ አቡነ ጴጥሮስ የሞታቸው ሰዓት መድረሱን ዐውቀው ሰዓታቸውን ከኪሳቸው አውጥተው ተመለከቱ ፡፡ ሰዓቱም 5፡15 ነበር ፡፡ በዚህ ጊዜ ሁሉ ምንም ፍርሃት አይታይባቸውም ነበር፡፡ የሞታቸውን ፍርድ ያነብ የነበረው ኢጣሊያዊ ዳኛ ግን ይንቀጠቀጥ ነበር ፡፡ ታላቅ ፍርሃትም በፊቱ ላይ ይታይ ነበር፡፡

ሐምሌ ፳፪ ቀን ፲፱፳፰ ፤ ፭፡፲፭ ሰዓት ለማስተካከል

ይሙት በቃ የተፈረደባቸው ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ በችሎት ፊት ለብዙ ሰዓታት ቆመው ስለዋሉና ደክሞአቸው ስለነበር ለመቀመጥ ፈልገው ዳኛውን በትሕትናና በፈገግታ ጠየቁት ፡፡ እንዲቀመጡም ፈቀደላቸው ፡፡ በመጨረሻም የሞታቸው ፍርድ ከተነበበ በኋላ የፈረዱባቸውን ዳኞች ጸልየው በመስቀላቸው ባረኩዋቸው ፡፡ ብፁዕነታቸው እስከ መቃብር አፋፍ ድረስ የፍርሃትና የድንጋጤ ምልክት ያይደለ ከልብ የሆነ ፍጹም ቆራጥነት ይታይባቸው ነበር፡፡

የሀገራቸው በጠላት መወረር፣ የሕዝባቸው መገደልና መታሰር፣ የቤተ ክርስቲያናቸው መደፈር እስከ ሞት ያደረሳቸው እኒህ እውነተኛ ጳጳስ ለመገደል ሲወሰዱ ጥይት አልፎ ሌላ ሰው እንዳይጎዳ ግንብ ይፈለግ ጀመር፡፡ ሩቅ ባለመሔድ ከመካነ ፍትሑ 10 ሜትር ርቆ ግንብ ያለው መግደያ ቦታ ተገኘና ወደዚያ ተወሰዱ ፡፡ ከገዳዮቹም አንዱ “ፊትዎን ለመሸፈን ይፈልጋሉን?” ሲል ጠየቃቸው ፡፡ “ይህ የአንተ ሥራ ነው” ሲሉ ብፁዕነታቸው መለሱ ፡፡ ከመግደያውም ቦታ እንደደረሱ ወንበር ቀረበላቸውና ፊታቸውን ወደ ግንቡ ጀርባቸውን ወደ ሕዝቡ አድርገው እንዲቀመጡ ሆኑ ፡፡

ከዚያ በኋላ ስምንት ወታደሮች በስተጀርባቸው ሃያ ርምጃ ርቀው ተንበርክከው በተጠንቀቅ ቆሙ ፡፡ ወዲያው አዛዡ “ተኩስ” በማለት ትእዛዝ ሲሰጥ ስምንቱም ተኩሰው መቱዋቸው ፡፡ ግን በስምንት ጥይት ሳይሞቱ ቀሩ ፡፡ መሞታቸውንና አለመሞታቸውን ለማረጋገጥ ዶክተር ተጠራ ፡፡ ዶክተሩም እንዳልሞቱ አረጋገጠ ፡፡ ከዚያም ሌላ ወታደር በሦስት የሽጉጥ ጥይት ራስ ቅላቸውን መትቶ ገደላቸው ፡፡ ብፁዕነታቸው የተገደሉበት ቦታ መኻል አዲስ አበባ ዛሬ መታሰቢያ ሐውልታቸው ቆሞ በሚገኝበት ቦታ አካባቢ ነው፡፡

“የብፁዕነታቸው አስክሬን ማንም እንዳይወስደው በአስቸኳይ ከአዲስ አበባ ውጭ ማንም በማያውቀው ቦታ በምሥጢር እንዲቀበር ተደረገ ፡፡ በዚያች ሌሊት በአዲስ አበባ ውስጥ በየቤቱ ልቅሶና ዋይታ ሆነ ፡፡”

ይህ ጋዜጠኛ የሰጠው ምስክርነት የብፁዕ አባታችን አቡነ ጴጥሮስን የመሪ ሀገር ወዳድነትና የኢትዮጵያን ሕዝብ ታጋሽነትና ጀግንነት ሲያረጋግጥ ይኖራል ፡፡

የብፁዕነታቸውን በድን በተመለከተ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያናችን አባቶች ቅዱሳን መላእክት የጻድቃንን በድን እያመጡ እንደሚያስቀምጡበትና በውስጡ የሚቀመጥ አስክሬን እንደማይፈርስ ወደሚነገርለት አቡነ መልከ ፄዴቅ ዋሻ /ሰሜን ሸዋ/ መላእክት ወስደው እንዳስቀመጡትና በዚያ እንደታዬ ይናገራሉ ፡፡

በተጨማሪም ደራሲና ጋዜጠኛ ጳውሎስ ኞኞ “አቡነ ጴጥሮስ እንዴት ሞቱ?” ሲል ሙሴ ፓይላክን ጠይቋቸው እርሳቸውም የሚከተለውን ተናግረዋል ፡፡

“አቡነ ጴጥሮስ የተገደሉ ዕለት እዚያው ነበርኩ ፡፡ መጀመሪያ በእጃቸው ይዘውት የነበረውን መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ተሳለሙት ፡፡ ቀጥለውም በያዙት መስቀል አማትበው ሕዝቡን ባረኩ ፡፡ የኪሳቸውንም ሰዓት አውጥተው ካዩ በኋላ መልሰው ከኪሳቸው ከተቱት ፡፡ ወዲያው ወታደሮች በሩምታ ተኩሰው ገደሉዋቸው ፡፡ ይህ እንደ ሆነ አስገዳዩ ኮሎኔል ተመልካቹን ሕዝብ አጨብጭቡ ብሎ አዘዘና ተጨበጨበ ፡፡

ማታ ከአስገዳዩ ኮሎኔል ጋር ተገናኝተን ስንጫወት:

“በዚህ ቄስ መገደል እኮ ሕዝቡ ተደስቷል” አለኝ፡፡ “እንዴት?” ብለው “አላየህም ሲያጨበጭብ” አለኝ ፡፡ እኔም “ባታውቀው ነው እንጂ የሕዝቡ ባሕል ሲናደድም ያጨበጭባል” አልኩት ፡፡ “እንዴት?” ቢለኝ እጄን እያጨበጨብኩ አሳየሁት ፡፡ እሱም አሳየኝ ፡፡ “ከዚህ በኋላ የሆነው ቢሆን እኔ ትልቅ ማስታወሻ አግኝቼአለሁ” ብሎ አቡነ ጴጥሮስ ሲገደሉ ይዘውት የነበረውን መስቀልና መጽሐፍ ቅዱስ ፣ የኪስ ሰዓታቸውን ጭምር አሳየኝ ፡፡ መጽሐፍ ቅዱሱ መሐል ለመሐል በጥይት ተሰንጥቋል ፡፡ መስቀሉም ልክ በመሐከሉ ላይ ጥይት በስቶት ወጥቷል፡፡ የኪስ ሰዓታቸውንም እንዳየሁት እንደዚሁ ጥይት በስቶታል” ብለው ያዩትን መስክረዋል ፡፡

የመታሰቢያ ሐውልት ለማስተካከል

የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ጥብአት ማለትም ለሀገራቸውና ለእምነታቸው እስከ መጨረሻዋ ሰዓት ድረስ መስክሮ ማለፍ ምክንያቱ በልጅነታቸው ከቅኔ መምህራቸው የሰሙት የአደራ ቃል እንደሆነ ይነገራል፡፡ አለቃ ተጠምቀ የተባሉ ቅድስናን ከሊቅነት አስተባብረው የያዙ መምህራቸው አንድ ቀን ብፁዕነታቸውን ጠርተው

“ኃይለ ማርያም፣ አንተ ወደ ፊት ጳጳስ ትሆናለህ፡፡ በዚያ ጊዜ አረመኔ በዚህች ሀገር ይሠለጥናል፡፡ ታዲያ ያኔ አንተ ለነፍስህ ሳትሰቀቅ በሰማዕትነት እለፍ፡፡ ሰማዕትነት ክፍልህ ነው፡፡ አደራ”

ብለዋቸው ነበር ይባላል፡፡ ይህንን የመምህራቸውን የአደራ ቃል የያዙት ብፁዕነታቸው እስከ መጨረሻው ለነፍሳቸው ሳይፈሩ፣ አንዲትም ቀን ሳይሸሹ ከላይ በቀረበው ሁኔታ የሰማዕትነት ጽዋቸውን ሊቀበሉ ችለዋል፡፡ ጠላት ድል ተደርጎ ሀገራችን ነፃነቷን ከተቀዳጀት በኋላ የብፁዕነታቸውን አኩሪ ታሪክ ትውልድ ሲያዘክርላቸው እንዲኖር መታሰቢያ ይሆናቸው ዘንድ በግርማዊ ቀዳማዊ ንጉሠ ነገሥት አሳሳቢነት ሐምሌ 16 ቀን 1938 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ እምብርት ሐውልት ቆሞላቸዋል፡፡ ከድል በኋላ የብፁዕነታቸው ሐውልት ተመርቆ የቤተ መንግሥቱም ሆኑ የቤተ ክህነቱ ባለሥልጣናት አበባ ጉንጉን ከሐውልቱ ሥር ሲያስቀምጡ ከቤተ ክህነት ካስቀመጡት አባቶች አንዱ በ1921 ዓ.ም አብረዋቸው የተሾሙት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ነበሩ፡፡ ትውልድ ሁሉ ለሀገር ክብርና ለነጻነት በተከፈለው፡፡ የብዕፁነታቸው ሕይወት እንዲማርበትና ሕያው ምስክር ሆኖ እንዲኖር የቆመላቸውን ሐውልት ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በክብር ይጠብቁታል ፡፡

የእኝህን ታላቅና ቅዱስ ሰማዕት አባት ክብርና ተጋድሎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከአምስት ዓመት በፊት ቅዱስ /ሰማዕት/ ብሎ በማጽደቅ በስማቸው በቅድስና ማዕረግን ሰጥቶ በስማቸው ታቦት ተቀርጾ ቤተክርስቲያን እንዲሰራላቸው ወስኗል ፡፡ ይህም  በተወለዱበት በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሃገረሰብከት በፍቼ ከተማ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተግባራዊ ሆኗል፡፡ ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ አርበኛ፣ ጀግና፣ ጳጳስ፣ ሰማዕት ቅዱስም የሆኑ አባት ናቸው ፡፡