ጌዴኦኛ ወይም ጌዴኡፋ በኢትዮጵያ ውስጥ በጌዴኦ ብሔረሰብ የሚነገር ኩሻዊ ቋንቋ ነው። የጌዴኦ ብሔረሰብ የአፍ መፍቻ ቋንቋ ሲሆን በብሔረሰቡ አባላት ጌዴኡፋ በመባል ይጠራል። ቋንቋው በተለይ ከሲዳምኛ፣ ከከምባትኛ፣ እና ከሀዲይኛ ቋንቋዎች ጋር የመመሳሰል ባህርይ አለው። በአሁኑ ሰዓት ጌዴኡፋ ከንግግር ቋንቋነት አልፎ የሥራ እና የትምህርት ቋንቋ ሆኖ እያገለገለ ይገኛል። በ፲፱፻፺፪ ዓ.ም. የሣባ ፊደል ተቀርፆለት ለመሠረተ ትምህርት ማስተማሪያነት ውሏል። ከ፲፱፻፹፮ ዓ.ም. ጀምሮ ግን ለቋንቋው የላቲን ፊደል ተቀርፆለት በርካታ የመማሪያና የማስተማሪያ መጽሐፍት ተዘጋጅተው መደበኛ ትምህርት በመስጠት ላይ ይገኛል። በአሁኑ ሰዓት በጌዴኦ ዞን ውስጥ በአብዛኛዎቹ በአንደኛ ደረጃ የመጀመሪያ ሣይክል ትምህርት ቤቶች ትምህርት የሚሰጠው በጌዴኡፋ ቋንቋ ሲሆን በሁለተኛ ሣይክል /ከ5ኛ--8ኛ/ ባሉት ክፍሎችም ቋንቋው እንደ አንድ የትምህርት ዓይነት በመሰጠት ላይ ይገኛል። ከዚህ በተጨማሪ ቋንቋው የሥራ ቋንቋ ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል። በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም. የጌዴኡፋ-አማርኛ-እንግሊዝኛ መዝገበ ቃላት ተዘጋጅቶ ለተጠቃሚው እንዲደርስ ተደርጎአል።

ዋቢ ምንጭ ለማስተካከል