ኢዩኤል ዮሐንስ ሰኔ ፳፩ ቀን ፲፱፳፯ ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ ተወለዱ። የቅኔ፣ የዜማና አቋቋም ትምህርትን በቤተ ክህነት፣ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በተለያዩ ትምህርት ቤቶች የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በማታው ክፍለ ጊዜ ከካቴድራል ትምህርት ቤት አጠናቀዋል፡፡


በለንደን ድራማ ማዕከል ሴንተር ልዩ የድራማ ኮርስ ተምረውና በሙያው ሠልጥነው በቴአትር ቤት አስተዳደር /ማኔጅመንት እና በመድረክ ዳንስ አቀናባሪነት ዲፕሎማና ሰርተፊኬት አግኝተዋል፡፡


ኢዩኤል ዮሐንስ ከ፲፱፴፭ ዓ.ም. ጀምሮ በኢትዮጵያ ሕዝብ የሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ውስጥ ከ 65 ያላነሱ ረዣዥምና አጫጭር ድራማዎችን፣ ኢትዮጵያዊ ኦፔራ፣ ሙዚቃዊ ድራማ፣ ልዩ ልዩ ግጥሞችን፣ ሽብሸባዎችን፣ የብሔርና ብሔረሰብ ዳንኪራና ጭፈራዎችን፣ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ መድረክ ማቅረብ የቻሉና ልዩ ስጦታ የነበራቸው የጥበብ ሰው ነበሩ፡፡


ኢዩኤል ዮሐንስ ዘፈኖችንና መዝሙሮችን ከላይ በተጠቀሰው ቴአትር ቤት፣ በብሔራዊ ቴአትር በሲኒማ ራስ፣ በወ.ወ.ክማ፣ በዩኒቨርሲቲ፣ በሁለተኛ ደረጃ ት/ቤቶች፣ በክፍላተ ሀገራት በሚገኙ አውራጃዎችና ወረዳዎች፣ እንዲሁም በቴሌቪዥንና በሬዲዮ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከማቅረባቸውም ባሻገር በአፍሪካ፣ በአውሮፖ፣ በእስያና በሩቅ ምሥራቅ አህጉራት መድረኮች ላይ በመገኘትም የኢትዮጵያን ባህል በስፋት አስተዋውቀዋል፡፡

የደራሲው ሥራዎች
 አቻ ጋብቻ(ተውኔት)
 ሥራ ለሠሪው(ተውኔት)
 ዘመን ሲለወጥ(ተውኔት)
 ይመሻል ይነጋል(ተውኔት)
 አያልነሽ(ተውኔት)
 የአርበኞች ዠግንነት(ተውኔት)
 የቸነፈር ዘመን(ተውኔት)
 የቆጡን አወርድ ብላ፥ የብብቷን ጣለች(ተውኔት)
 የእግዚአብሔር ቸርነት፥የአርበኞች ዠግንነት(ተውኔት)
 መንገደ ሰማይ(ተውኔት)
 ከእጅ አይሻል ዶማ(ተውኔት)
 ብቸኛ የሐሳብ ጓደኛ(ተውኔት)
 ያገር ፍቅር ትዝታው(ተውኔት)
 የልጃገረድ ሳሎን(ተውኔት)
 ሳይቸግር ጤፍ ብድር (ተውኔት)
 ማን ጠግቦሽ(ተውኔት)
 የሴት ፍርሃቷ እስከመቀነቷ(ተውኔት)

ምንጭ: የኢትዮዽያ ደራሲያን ማሀበር ለሚሊኒየም ያሳተመው አጀንዳ።

http://www.ethioreaders.com/authorbook.php?fl=364&lg=A