ቅዱስ ዮሴፍ በዕብራይስጥ: יוֹסֵף‎ ፣ በሮማውያን ማለት በላቲን : Yosef ፣ በግሪክ : Ἰωσήφ) በሐዲስ ኪዳን መጀመሪያ አካባቢ ስም አጠራራቸው ከከበረ ደጋግ እስራኤላውያን አንዱ የእመቤታችን ጠባቂ አረጋዊ ቅዱስ ነው ። ትውልዱ ከነገደ ይሁዳ ከንጉሥ ዳዊት ሲሆን አባቱ ያዕቆብ እናቱም ዮሐዳ ይባላሉ ።

ቅዱስ ዮሴፍ
ቅዱስ ዮሴፍ ከቅድስት ድንግል ማርያምና ከልጇ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋራ

የቅዱስ ዮሴፍ የሥራ መደብር
አረጋዊ ፃድቅ
የኖረው በመጨረሻዎቹ ዓ.ዓ. ና በመጀመሪያዎቹ ዓ.ም. በቤተልሄም በገሊላ በናዝሬት በኢየሩሳሌም
የሚከበረው በመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች
በዓለ ንግሥ ሐምሌ ፳፮ ቀን ዕረፍቱ ና ግንቦት ፳፬ ቀን ስደቱ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን)
ማርች ፲፱ (በምዕራባውያን ክርስትና)
ከክርስቶስ ልደት በኋላ የመጀመሪያው እሁድ (በምሥራቃውያን ክርስትና)

ቅዱስ ዮሴፍ ድግር ጠራቢ ነበር፤ ይህም ማለት ለእርሻ አገልግሎት በበሬ ለማረስ የሚያስፈልጉ ሞፈርና ቀንበር የሚሠራ ነበር ፡፡
በጉብዝናው ወራት የእመቤታችንን አክስት ማርያምን አግብቶ ብዙ ልጆችን ወልዶ አርጅቷል ። ከልጆቹም ዮሳ ፣ ያዕቆብ ፣ ይሁዳ ፣ ስምዖንና ሰሎሜ በቅዱስ መጽሐፍ ተዘክረዋል። ቅዱስ ዮሴፍ እድሜው ሰባ አምስት ሲሆን ሚስቱ ማርያም ሞተችበት ።
ባለቤቱ ካረፈች ከጥቂት ወራት በኋላም አይሁድ በምቀኝነት ድንግል ማርያምን ከቤተክህነት አስወጡልን ብለው ግብግብ በፈጠሩ ጊዜ "ልማ በሥሉስ ጥፋ በሥሉስ" እንዲሉ በሦስት ነገር ተመስክሮለት በመንፈስ ቅዱስ ምርጫ ድንግል ማርያምን ሊያገለግል ተመረጠ ። በወንጌልም "እጮኛ" የሚለውም ለዚያ ነው (የታጨው ለአገልግሎት ስለሆነ) ።
እመቤታችን ለአረጋዊ ዮሴፍ በሁለት ወገን ልጁ (ዘመዱ) ናት:

  • የሚስቱ ማርያም የእኅት (የሐና) ልጅ ናት ።
  • የቅድመ አያቱ የዓላዛር የልጅ ልጅ ናት ።

ደጉ ሽማግሌ ቅዱስ ዮሴፍ ምንም ቢያረጅ እመቤታችንን ለማገልገል አልደከመውም ። አብሩዋት ተሰዷል ፣ ረሐብ ጥማቷን ፣ ጭንቅና መከራዋን ፣ ሐዘንና ችግሩዋን ተካፍልዋል ። ከእመቤታችንና ከአምላክ ልጅዋ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ለ፲፮ ዓመታት አብሩዋቸው ኖርዋል ።
ቅዱስ ዮሴፍ በክርስትና ሃይማኖትም ሆነ በዓለማዊ ሕይወት ኑሮ ውስጥ ላሉ ሰዎች የምርጥ አባቶችና የጎበዝ ሠራተኞች ምሳሌ ነው ።
ያረፈውም በ፲፮ኛው ዓ.ም. በተወለደ በዘጠና አንድ ዓመቱ ነው ። ክርስቶስ የገነዘው አንድ ቅዱስ ቢኖር ቅዱስ ዮሴፍ ነው ። በዚህም ዕለት እግዚአብሔር የፅድቅ አክሊል አቀዳጅቶታል ።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

: