መቼት የሚለው ቃል ከ"መቼ" እና "የት" ከተሰኙ ሁለት የአማርኛ ቃላት የመጣ ሲሆን የጊዜኅዋዕን ጥምረት ያሳያል። ከድሮ ጀምሮ፣ ሰዎች ጊዜንና ህዋዕን በማዛመድ ተመልክተዋቸዋል። በተለይ ከአይንስታይን የልዩ አንጻራዊነት እና አጠቃላይ አንጻራዊነት ርዕዮተ አለሞች ወዲህ የጊዜና ኅዋዕ ጥምረት (መቼት) ለሳይንስ እንደመሰረታዊ ነገር ያገለግላል። በርዕዮቶቹ መሰረት፣ መቼት፣ በእንቅስቃሴ ምክንያት ከአንድ ተመልካች ወደሌላ ተመልካች የሚለያይ እንጂ በአንድ ዋጋ ለሁሉ ተመልካች አይጸናም። በርዕዮቶቹ መሰረት፣ ያለፈው ጊዜ የሚባለው ብርሃን ለአንድ ተመልካች መላክ የሚችሉ ኩነቶች (ክስተቶች) ስብስብ ሲሆን ፣ መጪው ጊዜ ደግሞ አንድ ተመልካች ብርሃን ሊልክባቸው ይሚችላቸው ኩነቶች ስብስብ ነው።