ዘረኝነት አንድ የህዝብ ወገን በውጫዊ ማንነቱ ብቻ የሚገለጥ ከሌሎች የሚበልጥበት ባህርይ አለው ብሎ የሚያምን አመለካከት ነው። ይህም ሌላውን ወገን በንቀትና በማጣጣል የሚያርቅ፣ የሚቃረንና ብሎም እስከ ማጥቃት (ማጥፋት) የሚዘልቅ ነው። አሁን ያለው ዘረኝነት የተመሠረተው በሰዎች ውጫዊ (ሥነ ሕይወታዊ) ልዩነት ላይ ነው። ለምሳሌ የቀለም ልዩነትን የዚህ አመለካከት አራማጆች በዋናነት ይጠቀሙበታል። ዘረኛው በማህበረ ሰብ ውስጥ በሁሉም መስክ የአንዱን ዘር ተፈጥሮአዊ የበላይነት በሌላው የበታችነት ለማረጋገጥ ተግቶ ይሠራል።