በዓሉ ግርማ

ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ እና ደራሲ
(ከበአሉ ግርማ የተዛወረ)

ደራሲ በዓሉ ግርማ በኢላባቡር ክፍለ ሀገር ሱጴ በምትባል ሥፍራ በ1928 ዓ.ም. ተወለዱ። ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በልዕልት ዘነበወርቅ ትምሕርት ቤት ፤ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በጄኔራል ዊንጌት ትምህርት ቤት አጠናቀዋል። ከዚያም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፖሊቲካል ሳይንስ እና ኢንተርናሽናል ሪሌሽንስ የ ቢ.ኤ. ዲግሪ ያገኙ ሲሆን፤ በዚሁ ተመሳሳይ መስክ ከአውሮፓ የማስተርስ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።

በዓሉ ግርማ (1928 - 1976 ዓ.ም.)

ደራሲ በዓሉ ግርማ በተለይ በልብ ወለድ እና በፈጠራ የሥነ ጽሑፍ ሥራዎች ከታወቁት የኢትዮጵያ የዘመኑ ደራሲዎች መካከል ተወዳጅነትና ዝናን ያተረፉ ዕውቅ ደራሲ ነበሩ። ከጻፏቸው በርካታ ድርሰቶቻቸው ውስጥ «ከአድማስ ባሻገር» የተሰኘው መጽሐፋቸው በሩስኛ ቋንቋ ተተርጉሞ በቀድሞዋ የሶቪየት ሶሽያሊስት ሪፑብሊኮች ኅብረት ቀርቧል። በተጨማሪም በጋዜጠኝነት ሙያም ስማቸውን ያስጠሩ፤ ሙያቸውንም ያስከበሩ ደራሲ ነበሩ። «የዛሬይቱ ኢትዮጵያ» ጋዜጣ፤ የመነን መጽሔት፤ የአዲስ ረፖርተር መጽሔት፤ የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በመሆን ከመሥራታቸውም ባሻገር፤ ብዙ ወጣት ጋዜጦችን ለማፍራት ጥረት አድርገዋል። አዲስ ሪፖርተር የተባለውን መጽሔትም ደረጃው ከፍ እንዲልና በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲገመገም አድርገዋል። በጋዜጠኝነት ሙያቸው በኢትዮጵያ ራዲዮ ሠርተዋል።

ደራሲ በዓሉ ግርማ ለኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱና ብዙ ሥራዎችን ያቀረቡ ሲሆን፤ የመጨረሻው መጽሐፋቸው «ኦሮማይ» በመባል ይታወቃል። ይኼውም መጽሐፍ በወቅቱ በነበረው የደርግ መንግሥት ሊደገፍ ባለመቻሉ በ1976 ዓ.ም. ለደራሲው ሕይወት መጥፋት መንስኤ ሊሆን በቅቷል። [1]

ድርሰቶች ለማስተካከል

  • ከአድማስ ባሻገር
  • የኅሊና ደወል
  • የቀይ ኮከብ ጥሪ
  • ሐዲስ
  • ደራሲው
  • ኦሮማይ

ማስታወሻ ለማስተካከል

  1. ^ ብሔራዊ ቢብሎግራፊ (የደራሲያን አጭር የሕይወት ታሪክ) 1998 ዓ.ም.