ቀዳማዊ ምኒልክኢትዮጵያ የመጀመሪያው ሰሎሞናዊ ንጉሥ ናቸው ተብሎ ይታመናል።

ደግሞ ይዩ ለማስተካከል

ቤተ እስራኤላውያን እነማን ናቸው?

ታሪኩን ለመረዳት ከጌታችን ልደት በፊት በእስራኤል ላይ ነግሦ የነበረውን የንጉሥ ዳዊት ልጅ የሆነውን የጠቢቡ ሰሎሞንን ታሪክ እና በኢትዮጵያ/በአቢሲኒያ የነገሠችውን የንግሥተ ሳባን ታሪክ ማየት ግድ ይለናል። እንድሁም ታራኩ ከታቦተ ፅዮን አመጣጥ ጋር ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት ያለው ሲሆን በመጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ ምዕራፍ 10 ላይ እና በሌሎች አዋልድ መጻሕፍት ላይ ተፅፎ እናገኜዋለን።

ጌታችን በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 12:42 ላይ "ንግሥተ ዓዜብ በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥታ ትፈርድበታለች፤ የሰሎሞንን ጥበብ ለመስማት ከምድር ዳር መጥታለችና" በማለት የጠቀሳት ንግሥተ ማክዳ ወይም ንግስተ ሳባ በወቅቱ የኢትዮጵያን/የአቢሲኒያን ሕዝብ የምታስተዳድር ንግሥት ነበረች፡፡ እንድሁም በጊዜው በእስራኤል ላይ ነግሦ የነበረውን የሰሎሞንን መንፈሳዊ ጥበብ በነጋደዎች በኩል ትሰማ ነበር። ዕለት ዕለትም የሰማችውን የሰሎሞንን ጥበብ እና ዝና ለማየት ትጓጓ ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ የሰሎሞንን ጥበብ በአካል ታይ ዘንድ፣ በእንቆቅልሽ ትፈትነው ዘንድ፣የሁለቱን አገራት ግንኙነት ታጠናክር ዘንድ በማሰብ ታምሪን በተባለ ነጋደ መሪነት ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ (መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ 10:1፤) ያለ አንዳች መሰናክልም ተጉዛ ኢየሩሳሌም ደረሰች፡፡ ለታቦተ ጽዮን ክብርና ለንጉሥ ሰሎሞንም ገጸ በረከት አቀረበች፡፡ ንጉሥ ሰሎሞንም እርሷንና ተከታዮቿን በጥሩ መስተንግዶ ተቀበላቸው፡፡ ንግሥት ሳባም የቤተ መንግሥቱን ሥርዓት ሥጋዊና መንፈሳዊ ጥበቡንም ሁሉ አስተዋለች። የጠየቀችውን እንቆቅልሽ ሁሉ ፈታላት፤ ሊፈታላት ያልቻለውና ከንጉሡ የተሰወረ ነገርም አልነበረም።" ንጉሡንም አለችው፦ "ስለ ነገርህና ስለ ጥበብህ በአገሬ ሳለሁ የሰማሁት ዝና እውነት ነው። እኔም መጥቼ በዓይኔ እስካይ ድረስ የነገሩኝን አላመንሁም ነበር፤ እነሆም፥ እኩሌታውን እንኳን አልነገሩኝም ነበር፤ ጥበብህና ሥራህ ከሰማሁት ዝና ይበልጣል።" አለችው። 1ኛ ነገሥት 10፥6-7

ንግሥተ ሳባ/ማክዳ በኢየሩሳሌም ቆይታዋ ከንጉሥ ሠሎሞን ቀዳማዊ ምኒልክን ፀነሰች፡፡ ወደ ኢትዮጵያም ተመልሳ ልጇን ምኒልክን ወለደች፡፡ ቀዳማዊ ምኒልክ በሀገሩ/በኢትዮጵያ ተወለዶ 12 ዓመት በሆነው ጊዜ ከእናቱ የተሰጠውን ለንጉሥ ሰሎሞንና ለታቦተ ጽዮን እጅ መንሻ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘ፡፡ ንግሥተ ሳባም ለንጉሥ ሠሎሞን “ንጉሥ ሆይ ልጄ ምኒልክ ሙሴ የጻፋቸውን ሕግጋትና ሥርዓተ ክህነት አስተምረህ ላክልኝ፡፡” የሚል መልእክትም አብራ ልካ ነበር፡፡ ቀዳማዊ ምኒልክም በኢየሩሳሌም ከአባቱ ዘንድ ለሦስት ዓመት ያህል የሙሴን መፃህፍት፣ ሕገ መንግሥትን፣ ሥርዓተ ክህነትንና የዕብራይስጥን ቋንቋ ከሊቀ ካህናቱ ከሳዶቅ እየተማረ ከቆየ በኋላ፤ ንጉሥ ሠሎሞን ልጁ ሮብኣም ገና ስድስት ዓመቱ ነበርና ምኒልክን አልጋ ወራሽ ሊያደርገው ቢያስብም ምኒልክ ግን ፈቃደኛ ስላልሆነና ወደ አገሩ ለመመለስ በመፈለጉ ምክንያት በካህኑ ሳዶቅ ቅብዓተ ንግሥ ተፈፅሞለት፤ ከአስራ ሁለቱም ነገደ እስራኤላውያን የተውጣጡ 12,000 ከሚሆኑ የእስራኤል ሌዋውያን ካህናት እና ከቤተመንግሥት ሹማምንቶች የበኩር ልጆች ጋር ወደ አገሩ/ኢትዮጵያ ላከው፡፡ የእስራኤል የበኩር ልጆችም ወደማናውቀው አገር ስንሄድ ታቦተ ፅዮንን ትረዳናለችና እሷን ሳንይዝ አንሄድም በማለት ተመካክረው የእግዚአብሔርም መልካም ፈቃድ ሆኖ ምንልክም ሆነ ሌሎች እስራኤላውያን ሳያውቁ በሙሴ እጅ የተቀረፀችውን ፅላት ይዘዋት ወደ ኢትዮጵያ መጡ፡፡ ንግሥት ሳባም ታቦተ ጽዮን መምጣቷን ስትሰማ ለእግዚአብሔር መስዋዕት አቀረበች፡፡ ሰዎችን መርጣ ታቦተ ጽዮንን እንዲጠብቁ አድርጋለች፡፡ የመንግሥቱን ሥልጣን በሙሉ ለቀዳማዊ ምኒልክ አስረክባ ከዚህ ዓለም በሞተ በተለየች ጊዜ በዚያው በአክሱም ተቀብራለች፡፡

ለእስራኤላውያን ብዙ ተአምራትን ያደረገች ይህችም ፅላት ለ3000 ዓመታት ያህል እስከዛሬ ድረስ በኢትዮጵያ በአክሱም ፅዮን ማርያም ትገኛለች፡፡

ታሪኩን ወደ ዋናው ርዕሳችን (ቤተ እስራኤላውያን) ስናመጣው እንድህ ነው። የመጀመሪዎቹ ቤተ እስራኤላዊያን ከእየሱስ ክርስቶስ ልደት በፊት ከንጉሥ ሠሎሞንና ከንግሥት ሳባ ልጅ (ከቀዳማዊ ምንልክ) ጋር ወደ ኢትዮጵያ የገቡ የእስራኤል የሹማምንቶች የበኩር ልጆች ናቸው። በጊዜው የሰፈሩትም በኤርትራ፣በአክሱም ትግራይ አካባቢዎች ይኖሩ የነበረ ሲሆን፤በኢትዮጵያ የክርሥትና ሃይማኖት የሀገሪቱ ብሔራዊ ሀይማኖት ሁኖ በታወጀበት ወቅት፣ የክርስትናን ሃይማኖትን አንቀበልም በማለታቸው ምክንያት ከአክሱም ተባረው በወገራ፣ ደምቢያ፣ ጭልጋ፣ ጣና ሀይቅ ዳር፣ እና በሰሜኑ ተራራማ ቦታዎች ሰፍረዋል። በህገ ኦሪት የሚመራ የራሳቸውን ስርወ መንግስትም አቋቁመዋል።