ፔኒሲሊን20ኛው ክፍለ ዘመን የተገኘ መድሃኒት አይነት ነው። በተፈጥሮ ፔኒሲልየም በተባለ ፈንገስ (ሽበት) ወገን የሚገኝ ሞለኪል ሲሆን ይኸው ሞለኪል ብዙ በሽታ አዘል ባክቴሪያ በማጥፋቱ እንደ ፀረ ባክቴሪያ ፈውስ በሰፊ ይጠቀማል።

የፔኒሲሊን ችሎታ መጀመርያ በድንገት የተገኘው በ1921 ዓም በስኮትላንድ ሳይንቲስት አሌክሳንደር ፍሌሚንግ ነበረ። በ2ኛው የአለም ጦርነት ጊዜ በጅምላ ተሠርቶ ይጠቀም ጀመር። በ1949 ዓም መጀመርያ ሰው ሰራሽ ፔኒሲሊን በማስተጻምር ተሠራ።

ከፈወሱት በሽቶች መካከል አባለዘር በሽቶች ጨብቱ እና ቂጥኝ ስለ ነበሩ፣ በአሜሪካና በፈረንጅ ምዕራባውያን አለም ውስጥ ከ፪ኛ አለም ጦርነት በኋላ ቀስ በቀስ «ወሲባዊ አብዮት» የተባለውን ኅብረተሠባዊ ለውጥ እንደ ገፋ ተብሏል። ቀድሞ እነዚህ አባለዘር በሽቶች ለመረን ሰዎች ዋና እንቅፋት ሆነው ነበር። በፔኒሲሊን እነዚህ በሽቶች እንደ ተሸነፉ መስሎአቸው የመረንነት ሃዋርዮች በድፍረት ይሰብኩ ጀመር። በተለይ ይህ መልእክት በ1970ዎቹ እ.ኤ.አ. (= 1962-1972 ዓም) በሚዲያ በማሰራጨታቸው ብዙ ትዳሮች በዚያን ጊዜ ተፈቱ። ሆኖም በሚከተሉት 1980ዎቹ እ.ኤ.አ. አዳዲስ ፔኒሲሊን የማይጠቅምባቸው በሽቶች በተለይም ኤድስ ስለ ተነሡ ይህ «አብዮት» ይቀዘቀዝ ጀመር።

ጥቂት ሰዎች ለፔኒሲሊን አለርጂ ስላለባቸው በሕክምና ሊቀበሉት አይቻልም።

የፔኒሲሊን ስያሜ ከፔኒሲልየም ፈንገስ ወገን ነው። የፈንገስ ስም ከሮማይስጥ /ፔኒኪሉም/ «ቀለም-ብሩሽ» መጣ፣ ይህ የፈንገሱ ዱኬ ሰንሰለት እንደ ጥርግ ስለሚመስል ነው።