የሎንዶን ታላቅ ቃጠሎእንግሊዝ ዋና ከተማ፣ ሎንዶን በ1658 ዓ.ም. የደረሰ ታላቅ ቃጠሎ ነው። በዚህ እሳት ወደ ፲፫ሺህ ቤቶች ወድመዋል።

እሳቱ የተነሳው ቅዳሜ እኩለ ሌሊት ላይ ካንድ ዳቦ ቤት ነበር። በዘመኑ የሚሰራበት የእሳት መቆጣጠሪያ ዘዴ፣ የሚቃጠለውን ቤት ከበው ያሉ ቤቶችን ማፈራረስ ነበር። እሳቱ የሚበላው ነገር ሳያገኝ ሲቀር በራሱ ጊዜ የበላውን በልቶ ይጠፋል። እሳት ተከላካዮች በዚህ መንገድ እሳቱን ሊያስቆሙ ሲሞክሩ፣ ከቤት ባለቤቶች ከፍተኛ ተቃውሞ ተነሳባቸው።

የነዋሪዎቹን ተቃውሞ በማጠፍ ቤቶቹ እንዲፈርሱ የማዘዝ ስልጣን ያለው የሎንዶን ከንቲባ ተጠራ። እርሱ፣ እሁድ ዕለት በቦታው በደረሰ ጊዜ እሳቱ ከዳቦ ቤቱ ወደ ሌሎች ቤቶች ተዛምቶ ነበር። ልምድ የነበራቸው እሳት ተከላካዮች የአካባቢው ቤቶች በቶሎ እንዲፈርሱ ከንቲባውን ሊያግባቡት ሞከሩ። ከንቲባው ግን ቤቶቹ የኪራይ ቤቶች ስለሆኑና ባልቤቶቹ በቀላሉ ስለማይገኙ የነሱን ፈቃድ ማግኘት ስለማይቻል እንዳይፈርሱ አደረገ። ታሪክ አጥኝዎች፣ ይህ የከንቲባው ወላዋይነት፣ ቀጥሎ ለደረሰው ውድመት ተጠያቂ ነው ይላሉ።

እሳትን በመፍራት በከተማው ሳር ክዳን ቤቶች እና ከእንጨት የተሰሩ ቤቶች የተከለከሉ የነበር ቢሆንም፣ ብዙ ሰዎች በህገዎጥ መንገድ እንዲህ ዓይነት ቤቶች ነበሯቸው። በከተማይቱ ውስጥ ከፍተኛ የጥይት ባሩድ ክምችት ነበር። እንዲሁም አብዛኞቹ ቤቶች ተጠጋግተው የተሰሩ ነበሩ። ሌሎች ተቀጣጣይ ዘይቶች፣ ሙጫዎች ወዘተ ተደማምረው፣ የተነሳው እሳት በከፍተኛ ፍጥነት ከቦታ ወደ ቦታ እንዲዛመት አደረገ።

በዚህ መንገድ እሳቱ ለ፬ ቀናት በመንደድ፣ ከ80,000 የከተማው ነዋሪ የ70,000 ውን መኖሪያ አወደመ። በአራተኛው ቀን፣ እሳቱን የሚያራግበው ነፋስ ጋብ ብሎ፣ በከተማው ዙሪያ በንጉሱ ወንድም ት ዕዛዝ የፈረሱ ቤቶች እሳቱን ሲከቡት፣ መዛመቱ ቆመ። በሚቀጥለው እሁድ ዝናብ ሲጥል ሙሉ በሙሉ እሳቱ ጠፋ።

የሎንዶን ከተማ በ1608 ዓ.ም. ከመቃጠሏ ፶ ዓመታት በፊት።