የለጥ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት፤ በከሰም ወረዳ ውስጥ የሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ነው።

የለጥ
ጥቅምት ፳፫ ቀን ፳፻ ዓ.ም. የተመረቀው አዲሱ ቤተ ክርስትያን
ከፍታ 2028
የለጥ is located in ኢትዮጵያ
{{{alt}}}
የለጥ

9°12′ ሰሜን ኬክሮስ እና 39°19′ ምሥራቅ ኬንትሮስ

ማረጋገጫ ጽሑፍ ባይገኝም፤ አፈ ታሪኩ፣ የጊዮርጊስ ታቦት በቡልጋ የለጥ የተተከለው በዓጼ ዮሐንስ ዘመን ነው ይላል። እስከ ፲፱፻፵፫ ዓ.ም. ድረስ የቤተ ክርስቲያኑ ሕንጻ ክብ የሳር ክዳን ሕንጻ እንደነበር ይነገራል። እስከ እዚያም ዘመን የሰማእቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦት ከድንግል ማርያምቅዱስ ፋሲለደስ እና መድሃኔ ዓለም ታቦታት ሌላ 13 ታቦታት እዚያው እሳር ክዳን ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ እንደነበሩ ይነገራል።

፲፱፻፵፫ ዓ.ም ንቦች ጣሪያው ውስጥ ሰፍረው ኖሮ ከሳር ክዳኑ ውስጥ ሲገቡ ሲወጡ ይታዩ ነበር። የጊዜውም ካህናት በምስጢር ይሸራረሩኩና ማሩን በድብቅ ለመቁረጥ ይስማማሉ፣ ከዕለታት አንድ ቀን በምሽት ፍም ይዘው ሳር ክዳኑ ላይ ይወጡና ማሩን ቆርጠው ይወርዳሉ፣ ያልተገነዘቡት ግን ፍሙ ለካ እጣራው ወራጅ ላይ ወድቆ ኖሮ አንድ ሳምንት ሙሉ ካፈጋ በኋላ ተያይዞ ቤተ ክርስቲያኑን ያቃጥለዋል። ቤቱ ሲቃጠል የዋንዛ ዋልታው እመንበሩ ላይ ይወድቃና ታቦቱን ሸፍኖ ቀብሮ ያድነዋል። በየለጥ አካባቢ ሀዘንና ትካዜ ሰፈረ፣ ሕዝቡ ታቦታቱን ሲፈልግ ሰንብቶ በዚያ ጊዜ ከነበሩት አሥራ ሰባት ታቦታት ውስጥ የጊዮርጊስ ታቦትና የማሪያም፣ የመድሃኔዓለም፤ የፋሲለደስ ታቦታት ብቻ ሳይቃጠሉ ድነው ተገኙ ይላሉ ቄስ ሰርጸወልድ ተሰማ።

ይኸኔ ልዩ ስሟ ቡሄ አምባ በምትባለው የየለጥ መንደር በ ፲፱፻፯ ዓ.ም ተወልደው በአምስቱ የኢጣሊያ ዘመን በአርበኝነት ተሰማርተው ሀገራቸውን ያገለገሉት ደጃዝማች ኪዳኔ ወልደመድኅን ቤተ ክርስቲያኑን እንዲያሰሩላቸው ጠይቀዋቸው ደጃዝማች ኪዳኔም ቤተ ክርስቲያኑን አሰርተው ከጨረሱ በኋላ ሕንጻው አሰራሩ ቅሬታ ስላሰማቸው አስፈርሰው እንደገና አሰርተው ታቦቱን ሚያዝያ ፳፫ ቀን ፲፱፻፵፱) ዓ.ም አዲሱ ቤተ ክርስቲያን ሊያስገቡ ቻሉ። ይኼ ቤተ ክርስቲያን በዘማናዊ መልክ በአራት ማእዘን ተሰርቶ በአካባቢው ቡልጋ ውስጥ በቆርቆሮ የተሰራ የመጀመሪያው ሕንጻ ነበር።

፲፱፻፵፱ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፺፭ ዓ.ም ያገለገለው ደጃ/ኪዳኔ ወልደመድኅን ያሠሩት ሕንጻ

፲፱፻፺፭ ዓ.ም ለሚያዝያ ጊዮርጊስ በዓል በተደረገው የሕንጻ ምርመራ ቤተ ክርስቲያኑ አርጅቶ ተሰናጣጥቆ፣ ተበላሽቶ ስለነበር ሕንጻውን አፍርሶ እንደገና በዘማናዊ መልክ ለማሠራት ተወሰነ። ለዚኽም ሥራ:-

  • (ሀ) ገበሬው አሸዋ ከከሰም ወንዝና ከአማሪት ወንዝ፤ ድንጋይ ከልዩ ስሙ በር ከሚባለው ሠፈር ፈንቅለው በሰው ትከሻና በአህያ ሸክም
  • (ለ) ሲሚንቶ፤ የሕንጻ ብረት፤ ግንበኞችና ሌላም የሕንጻ ሥራ ባለሙያዎች ከአዲስ አበባ እስከ ሐሙስ ገበያ (አንዳንዴም እስከ ኮረማሽ) ድረስ በጭነት መኪና ተጉዞ ከዚያ በታች በሰው ሸክምና በአህያ ጭነት እስከ ቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ይቀርባል።
  • (ሐ) በዚህ ቆላ አካባቢ የውሐ እጥረት ስላለ ከቤተ ክርስቲያኑ በላይ አንድ ኪሎሜትር ርቀት ያለው ምንጭ ተገኝቶ ሦሥት ሜትር ተኩል በሁለት ሜትር ስፋት እና የ ሁለት ሜትር ጥልቀት ያለው ማቆሪያ ከተገነባ በኋላ የተጠራቀመውን ውሐ በ ፔትሮል ፐምፕ እየተሳበ በላስቲክ ቧንቧ ቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ድረስ ገብቶ ለሥራው አገልግሏል።

አዲሱ ቤተ ክርስቲያን ባለ ስምንት ማእዘን ሕንጻ ሲሆን፤ የመሬቱን ገደላማነት በመጠቀም ግምጃ ቤትና ቢሮ የሚሆን ምድር ቤት ተሠርቶለታል። ሕንጻው ሙሉ በሙሉ በድንጋይ የተገነባ ሲሆን፤ ጣራውን በዘመናዊ ሸክላ መሰል ቆርቆሮ ተደፍኗል። ከአካባቢውም ጋር በቀለም እንዲዋሃድ አረንጓዴ ቀለም ተመርጧል። ደጃዝማች ኪዳኔ ያሠሩት ቤተ ክርስቲያን ተገጥመው የነበሩት የሙገሬ ጽድ መዝጊያና መስኮቶች ከታደሱ በኋላ አዲሱ ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ተመልሰው ሊገጠሙ ችለዋል። ሥራው በሁለት ዓመት ተኩል ተጠናቆ ቅዳሜ ጥቅምት ፳፫ ቀን ፳፻ ዓ.ም ታቦታቱን አዲሱ ቤተ ክርስቲያን አስገብተናል። በዚህም ዕለት ጸበሉን አስባረክን።

ኢትዮጵያዊ የገጠር ሕዝብ በአንድነት የጋራ ኃይማኖቱን፤ ባህሉንም ሆነ ሰብዓዊ ሕይወቱን የሚኖረው በኃይማኖቱ ማስተናገጃ ቤት ነው። እነሆ በጋራ የዚህን ገጠር ሕዝብ "የለጤ" እና ሕዝበ ክርስቲያን አስብሎ የሚያስጠራውን የየለጥ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በቅድሚያ ተሠርቶለታል፤ ከዚህ በኋል ትምህርት ቤት፤ ክሊኒክ፤ ወዘተ. ሊከተል ይችላል። ይኼንንና የመሳሰሉትንም ተግባራት ለማስፈጸም እግዚአብሔር ፈቃዱ ይኹን።

አዲሱ ቤተ ክርስትያን እቡልጋ ተራራዎች መኻል