ዜቡልብሉይ ኪዳን መጽሐፈ መሳፍንት 9:28-41 መሠረት በእስራኤል ንጉሥ አቢሜሌክ ዘመን (1251-1249 ዓክልበ. ግድም) የሴኬም ከንቲባ ነበረ። የሴኬም ሰዎች በገዓል መሪነት በአቢሜሌክ ላይ ባመጹበት ጊዜ፣ ዜቡል መረጃውን ለአቢሜሌክ ያስረዳው ነበር።

ገዓል የአቢሜሌክ ሠራዊት ከተራራ ሲወርድ አይቶ ለሴኬም ከንቲባ ዜቡል ሲያጠቆም (መሳፍንት ፱፡፴፯)

ሌላ ዜቡል በጥንታዊ የአይሁዶች ታሪክ ከ62 ዓም አስቀድሞ በተጻፈው «የመጽሐፍ ቅዱስ ጥንታዊነት» (ሮማይስጥ፦ Liber Antiquitatum Biblicarum) ይጠቀሳል። በዚህ ታሪክ ዘንድ፣ የእስራኤላውያን መሪ ኢያሱ ወልደ ነዌ ካረፈ በኋላ፣ ቄኔዝም ለ57 ዓመታት እስራኤላውያንን ከመራቸው በኋላ፣ ዜቡል እንደ እስራኤል መሪ ወይም ፈራጅ ተመረጠ። ስለ ዜቡል 25 ዓመት አገዛዝ (1530-1505 ዓክልበ. ያህል) አንድ አጭር ምዕራፍ ይጽፋል።

የተዘገቡለት ድርጊቶች ጥቂት ናቸው። መጀመርያው ለቄኔዝ ሦስት ሴት ልጆች ሰፊ ርስቶች አካፈለላቸው። ዜቡልም ለያህዌ አንድ ግምጃ ቤት አቁሞ 20 መክሊት ወርቅና 250 መክሊት ብር ከሕዝቡ ተቀበለ። የጣኦታት ወርቅ ወይም ብር ግን አይቀብልም ነበር።

የዕረፍቱ ጊዜ ሲቀርብ ለሕዝቡ እንዲህ ብሎ ተናገረ፦ «ከኛ ቀድሞ የሆኑት ሰዎች የመሠክሩትን ምስክሮች ተመልከቱ። ልባችሁ እንደ ባሕሩ ማዕበል አይሁን፤ ነገር ግን የባሕሩ ማዕበል በባሕሩ ውስጥ ካለው በቀር እንደማያውቅ፣ እንዲህ ልባችሁ በሕግ ቅዱስ ውስጥ ካለው በቀር በምንም አያስብ።»

ከዚህም በኋላ እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ፊት እንደገና ክፉ ሆኑና በሓጾር ንጉሥ ኢያቢስ ስር ለ20 ዓመታት ተገዙ። ስለዚህ፣ ይህ ሰነድ በመጽሐፈ መሳፍንት የተጠቀሱትን የኲሰርሰቴም (8 አመታት)፣ የጎቶንያል (40 ዓመታት)፣ የዔግሎም (18 ዓመታት)፣ እና የናዖድ (80 ዓመታት) ዘመናትን ይዘልላል። በመጽሐፈ መሳፍንት የኲሰርሰቴም ዘመን ኢያሱ ካረፈ በኋላ ባልተወሰነ ጊዜ ሆነ። ስለዚህ ስለ ቄኔዝና ዜቡል ዘመኖች ያለው ትዝታ ትክክል ከሆነ፣ እነዚህ 82 ዓመታት ከኢያሱ በኋላ እና ከኲሰርሰቴም በፊት (1587-1505 ዓክልበ.) መሰካት ነበረባቸው።