ኢድሪሚ ከ1473 እስከ 1443 ዓም ያህል ድረስ የሙኪሽ አገር (አላላኽ ከተማ) ንጉሥ ነበረ።

የኢድሪሚ ሐውልት

የኢድሪሚ ታሪክ በተለይ ከሐውልቱ አካድኛ ጽሑፍ የሚታወቀው ነው። የሐለብ መጨረሻ ንጉሥ የ1 ኢሊም-ኢሊማ ልጅ ነበር፣ ይህም ሥርወ መንግሥት ቀድሞ የያምኻድ መንግሥት ተብሎ ነበር። በ1480 ዓክልበ. ገደማ የሑራውያን ንጉሥ ባራታርና ሐለብን ወደ ሚታኒ መንግሥት እንደ ጨመረው ይታመናል። ኢድሪሚና ቤትሠቡ ከሐለብ ወደ ኤማር ሸሹ። ኢድሪሚ ከዚያ ወደ ከነዓን ምድር አሚያ ከተማ ሂዶ ከሐቢሩ ወገን ጋር ለሰባት ዓመት ቆየ ይላል። በዚያ በስደት ሆኖ ከሐቢሩና ሐገሩ ስደተኞች መካከል ሥራዊት ያሕል ሰበሰበ። በ1473 ዓክልበ እነርሱ በመርከብ በሶርያ ተመልሰው ደረሱ፣ አላላኽን ለመያዝ ቻሉና የአላላኽ፣ የኑሓሼና የኒያ ኗሪዎች ተደሰቱ፤ ሙኪሽ ከተባለው አገር ጋር ተባበሩ ይላል። ባራታርና ግን ለሰባት ዓመት ጠላቱ ሆነ። በመጨረሻ በ1465 ዓም አካባቢ ኢድሪሚ መልክተኛውን ወደ ባራታርና ልኮ «እኛ ዱሮ የሑራውያን ጓደኞች ነበርን» በሚል መልዕክት አሳሰበው። ባራታርና ይህን ተቀበለና ኢድሪሚ ለሚታኒ ጥገኛ ንጉሥ ሆኖ በሙኪሽ እንዲቆይ ፈቀደ። ኪዙዋትና የተባለው አገር ደግሞ የሚታኒ ጥገኛ እንደ ተደረገ ይመስላል። በኢድሪሚም ሆነ በባራታርና ቅርሶች እስካሁን በተገኙት መረጃዎች ምንም ስለ ግብጽ ባይጠቀስም፣ ፈርዖን 3 ቱትሞስ ደግሞ በዚህ ዘመን በሙኪሽና በሚታኒ ላይ ይዘምት ነበር።

ከዚህ በኋላ ኢድሪሚ በሐቲ (የኬጥያውያን መንግሥት) ላይ ዘምቶ ሰባት አምባዎች እንደያዘባቸው ይላል። ከዚያ ሕዝቡን በጸጥታ አስተዳደረው ይላል። ጸሓፊውም ሻሩዋ ኢድሪሚ ለ30 አመት እንደ ገዛ በማለት ጨመረ።

ለኢድሪሚ ሁለት ሌሎች ጽላቶች ይታወቃሉ። ከነዚህ አንዱ ከኢድሪሚና ከኪዙዋትና ንጉሥ ፒሊያ መካከል የተደረገው ውል ነው። በዚህ ውል መሠረት ከአንዱ አገር ወደ ሌላው የሸሹት ባርዮች እንዲመለሱ አስቻለ። ባርያውን የያዘው ሰው 500 ሰቀል መዳብ ለወንድ፣ 1000 ለሴት ባርያ እንዲከፈል አዘዘ። ወይም የባርያው ጌታ እራሱ ባርያውን ለመያዝ እርስ በርስ ወደ ኪዙዋትናም ሆነ ሙኪሽ መግባቱን በነጻ ፈቀደው።

ኢድሪሚ ብዙ ጣኦታት እንዳገለገለ ስለ ጻፈ በእርግጥ አረመኔ ንጉሥ ነበር። በከነዓን ውስጥ ቢቆይ ብሉይ ኪዳንእስራኤል ውጭ በዚህ ዘመን ለነገሡት አረመኔ ነገሥታት ብዙ ትኩረት አይሰጥም፤ ግን ጎቶንያል ፈራጃቸው የሆነበት ወቅት ያሕል ይመስላል።

የኢድሪሚ ልጅ ኒፕመቃ በሙኪሽ ዙፋን ላይ ተከተለው።