ባራታርና እንደሚታመን ከ1 ሹታርና ቀጥሎ በሑራውያን ላይ የነገሡት የሚታኒ መሣፍንት ንጉሥ ነበር። እንዲህ ከሆነ ዘመኑ ምናልባት 1480-57 ዓክልበ. ያሕል ነበር።

ስሙ በተለይ የሚታወቀው በአላላኽ (ሙኪሽ አገር) ንጉሥ ኢድሪሚና በኪዙዋትና ንጉሥ ፒሊያ መካከል በተደረገው ስምምነት ውል ውስጥ እንዲሁም በኢድሪሚ ሐውልት ላይ ሲታይ ነው። በዚህ መሠረት ባራታርና ንጉሥ ሲሆን የያምኻድን ቅሬታ በሐለብ ያዘ፣ የሐለብም አልጋ ወራሽ ኢድሪሚ ወደ ሐቢሩ ወገን ሸሽቶ ከሰባት ዓመት ስደት በኋላ በርዳታቸው በኩል አላላኽን ለመያዝ ቻለ። ሆኖም አላላኽ ለባራታርና ተገዥ እንዲሆን እንደ ፈቀደ ይጠቀሳል። የባራታርና አርእስት «የሑራውያን ሥራዊት ንጉሥ» ተብሏል። የባራታርና ግዛት ወደ ምሥራቅ እስከ ኑዚና እስከ አራፕኻ ድረስ እንደ ዘረጋ ይባላል።

በኑዚ በተገኘ ሰነድ፣ የሚታኒ ንጉሥ ፓርሻታታር (ወይም ፓርሻታር) ባረፈበት ዓመት እንደ ተጻፈ፣ ሻውሽታታርም እንደ ተከተለው ይላል። በብዙዎች አስተሳሰብ ይህ ፓርሻታር እና ባራታርና (ፓራታርና) አንድ ንጉሥ ነበሩ። ሌሎች ግን የተለያዩ ነገሥታት ነበሩና ባራታርና ከፓርሻታታር ቀደመው የሚሉ ናቸው።

ግብጽ ፈርዖን 3 ቱትሞስ የመጊዶ ውጊያ በ1465 ዓክልበ.ግ. ተዋግቶ በ«ናሓሪን» (ሚታኒ) ላይ ሲዘመት የሚታኒው ንጉሥ ስም ባይዘገብም በሰፊው በሚገኘው ዘመናዊ አስተያየት ዘንድ ይህ ዘመቻ የባራታርና (ወይስ የፓርሻታታር) ዘመን ውስጥ ሆኖ ነነር።