ሐማዚ ምናልባት በ2420 ዓክልበ. ገዳማ የነበረ መንግሥት ሲሆን በምዕራብ ዛግሮስ ተራሮች ከኤላምና ከአሦር መካከል እንደተገኘ ይታሥባል።

ሐማዚ ለሥነ-ቅርስ ጥናት መጀመርያ የታወቀው በዚህ ቦታ ላይ የኪሽ ንጉሥ ኡቱግ ወይም ኡሁብ ድል የሚመዝገብ በጥንታዊ ባለ-ማዕዘን (ኩኔይፎርም) ጽሕፈት የተጻፈ ጽላት ሲገኝ ነበር።

ሌላ ጥንታዊ ጥቅስ ደግሞ ኤንመርካርና የአራታ ንጉስ በተባለ አፈ ታሪክ ተገኝቷል። እዚህ ኡሩክኤሪዱ ግንቦች በተሠሩ ጊዜ ስለ ልሣናት መደባለቅ የተለያዩ አገራት ሲዘረዘሩ በመዝሙር ይጠቀሳል። በዚሁ ዝርዝር፣ ሐማዚ ብቻ «ባለ ብዙ ልሳናት» የሚል ስያሜ ይሠጣል። የሚከተለው ጽሑፍ ኤንመርካርና ኤንሱህከሽዳና እንደሚለው፣ ሐማዚ ከጠፋ በኋላ የሐማዚው ጠንቋይ ኡርጂሪኑና ወደ አራታ ፈልሶ፣ ከዚያ የአራታ ንጉሥ ኡሩክን ለማሸነፍ በኤንመርካር ላይ ልኮት አልተከናወነም።

ሱመር ነገሥታት ዝርዝር መሠረት የሐማዚ ንጉሥ ሀዳኒሽ ኪሽን ካሸነፈ በኋላ (2243 ዓክልበ. ግ.) በሱመር ላይ ላየኛነት ያዘ። እሱ ግን በተራው በ2215 ዓክልበ. ግ. በኡሩክ ንጉስ በኤንሻኩሻና ድል ሆነ።

ኤብላ ከተማ በሶርያ በተገኘ የሸክላ ጽላት ላይ አንድ ዲፕሎማቲካዊ መልእክት ከኤብላ ንጉስ ኢርካብ-ዳሙ (2110 ዓክልበ. ግ.) ወደ ሐማዚ ንጉስ ዚዚ ከብዙ ዕንጨት ጋር ተላከ። እንደ ወንድም ሆኖ ሰላምታ ሰጥቶ በምላሽ ወታድር እንዲልክለት ይጠይቀዋል።

በአዲስ ሱመራዊ ኡር መንግሥት ጊዜ በንጉስ አማር-ሲን ዘመን (1918-1909 ዓክልበ.) ሐማዚ ከጠቅላይ ግዛቶቹ አንድ ነበር። በዚህ ዘመን የአገረ ገዥ ስሞች ኡር-ኢሽኩር እና የናምሃኒ ልጅ ሉ-ናና ይታወቃሉ። የኡር መንግሥት ሊወድቅ ሲል (1879 ዓክልበ. ገዳማ) ጠቅላይ ግዛቱን የኢሲን አለቃ ኢሽቢ-ኤራ ወረረው።